ቅንጅት የፈረሰበትን ምክንያት ለመናገር እንደማይፈልጉ ወ/ት ብርቱካን አስታወቁ

EPA : የቀድሞው የቅንጅት ለአንድነትና ለዴሞክራሲ አመራር የነበሩት ወ/ት ብርቱካን ሚዴቅሳ ቅንጅት የፈረሰበትን ትክክልኛ ምክንያት ለመናገር አልፈልግም አሉ።

ወደ አገር ቤት ከተመለሱ በሁዋላ ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጋር ሰፋ ያለ ቃለ መጠይቅ ያደረጉት ወ/ት ብርቱካን፤ “ቅንጅት የፈረሰበት ትክክለኛ ምክንያት ምንድን ነበር?” ተበለው ተጠይቀው በሰጡት ምላሽ፤ “እውነት ለመናገር አሁን ይሄንን ጥያቄ ልመልስ አልፈልግም፡፡ ልመልስ የማልፈልገው መልስ ስለሌለኝ ወይም ደግሞ ምክንያቱን ስላማላውቀውና ስለማልችል አይደለም” በማለት ምክንያቱን ከመግለጽ ተቆጥበዋል።

ወ/ት ብርቱካን አያይዘውም፤ “እስካሁንም የተነሱትን ነገሮች ሚዲያ ላይ አይቻለሁ፡፡ አሁን አገራችን ከሁላችንም አፋጣኝ ምላሽ የምትፈልግበት ወቅት ነው፤ ከዚያ ይልቅ ሌሎች በጣም አንገብጋቢ ጥያቄዎች አሉ” በማለት የግል አቋማቸውን ግልጽ አድርገዋል።

ከዚህ በፊት በነበረን ነገር ማን ጥፋተኛ ነው ፤ ማን የበላይ ነው? ማን የበታች ነው? ማንነው ያፈረስው? ለምን ፈረሰ? የሚለውን ነገር የአካዳሚክ ጥናት ለሚያደርጉ ሰዎች በጣም ጥሩ የጥናት መስክ ሊሆን ይችላል ያሉት ወ/ት ብርቱካን “አሁን እኔ በዚያ ንትርክ ላይ የመሰማራት ፍላጎት የለኝም፡፡ ለህብረተሰባችንም ዋና ጉዳይ ነው ብዬ አልወስደውም” ሲሉ ገልጸዋል።