እድሜ፣ ልምድ እና መከራ ካልመከረን የጎደለን ሌላ ነው ማለት ነው – ኡስታዝ አቡበከር አሕመድ

እድሜ፣ ልምድ እና መከራ ካልመከረን የጎደለን ሌላ ነው ማለት ነው – ኡስታዝ አቡበከር አሕመድ

እድሜ ብቻውን መካሪ ቢሆን ኖሮ በሞት አፋፍ ላይ የደረሱ አዛውንቶች ከጥፋት ገደል ገብተው አናይም ነበር። ልምድ ለችግራችን በቂ መፍትሄ ቢሆን ኖሮ የብዙ በዳዮችን መጨረሻ ያዩ፣ በሀገራችንም በአፍሪካም ስላለፉ ድንበር አላፊዎች በአካል የተመለከቱቱ መጨረሻቸውን ለማሰብ ሌላ ልምድ ባላስፈለጋቸው ነበር። በመከራ ከሚኖር ህዝብ ወጥቶ፣ መከራ ውስጥ የነበረችን ሀገር ሲመራ እና በስተመጨረሻም የመከራ ጥጎችን ሲያይ ወደቀናው ለመመለስ በቂ በሆነ ነበር።

የጎደለን ሌላ ነው። ሰው ሆኖ እንደሰው የማሰብ ጉድለት ነው ችግራችን። በሰፊ ሀገር ውስጥ እየኖርን የመጥበብ ችግር ነው ያጋጠመን። ለሁሉ በሚበቃ ምድር በሌላው መቃብር ካልሆነ እኔ ልቀበር ባይነት ነው የቀበረን።

የቀናት መፈራረቅ የፈጣሪ ሱና ነው። የነገራቶች መስተካከል ግን የፍጡራንን ፍላጎት ይፈልጋል። አሁንስ ምንድን ነው የምንፈልገው? የምንደክመው? በከተማ የምናስተዳድረው? የምንመራው? በበረሃ የምንዋጋው? ስለምን ስንል ነው? ፍላጎታችን ሀገርና ህዝብ ከሆነ የግል እብሪትና በሬሳዬ ላይ ካልሆነ የምንልበት ገደብ ይኖረዋል። ፍላጎታችን ሀገር እና ህዝብ ከሆነ ካለፈው የምንማረው ያለፈውን በመርገም ሳይሆን ዋ ለራሴ በሚል እሳቤ ነው። ፍላጎታችን ሀገርና ህዝብ ከሆነ ተራ በተራ መጨረሻው የማያምር መሆናችንን አስቀርተን የጥፋት መዳረሻ መንገዶችን መጨረሻቸውን ለመፈለግ ቃል በመግባት ነው። ኡስታዝ አቡበከር አሕመድ