ሱዳን ያላት አቋም በፍትሃዊነት ላይ የተመሰረተ ስለሆነ ልናደንቃት ይገባናል – አምባሳደር ዲና ሙፍቲ

👉የህዳሴው ግድብ የመሰረት ድንጋይ ከተጣለበት ጊዜ ጀምሮ የግብፅ መንግስት ከፍተኛ ገንዘብ በመመደብ በተለያዩ ሀገራት በመንቀሳቀስ ኢትዮጵያን ለማሳጣት “ኢትዮጵያ ልታስጠማን ልታስርበን ነው”ነው በማለት የተለያዩ የሃሰት ፕሮፓጋንዳ አራግበዋል፤
👉 ግብጾች በአሜሪካና አዉሮፓ ሀገራት በመዘዋወር “ግብጽ መቶ ሚሊዮን ህዝብ አላት፣ ይህን ያህል ህዝብ የያዘችን አገር ኢትዮጵያ የውሃ ድርሻዋን ለመከልከል እየሰራች ነዉ፣ ኢትዮጵያ ይህን ግድብ እውን ካደረገች የግብጽ ህዝብ መጥማቱና መራቡ አይቀርም፤ ይህ ደግሞ አሸባሪነትን ያስፋፋል፣ አሸባሪነት ሲስፋፋ ደግሞ በጋራ ያለንን የሰላም ህልዉናችንን ጥያቄ ዉስጥ ያስገባዋል፤ ታዲያ ይህ እንዳይከሰት ኢትዮጵያን ይህን ግድብ እንድታቆም ማድረግ አለባችሁ” በማለት ሲያስፈራሯቸዉ ቆይተዋል፡፡
👉በተመሳሳይ ግብጿዊያን በየጊዜው በዓረብ ሀገራት በመንቀሳቀስ ፣ “ኢትዮጵያ በግብፅ ህዝብ ላይ ግፍ እየሰራች ነዉ፡ ግብጾች ዓረብ በመሆናቸው ብቻ የዉሃ ሀብታቸዉን እንዳይጠቀሙ ሊደረጉ ነው። አረቢቷን አገር ዉሃ መከልከል ደግሞ የዓረቡ ዓለም ህልዉና መንካት ማለት ነዉ፡፡” በማለት የዓረቡን ዓለም በኢትጵያ ላይ ለማነሳሳት ኢትዮጵያን ለማስጠላት ሲሰሩ ቆይተዋል። ይሁንና ኢትዮጵያ የግብፅንም ሆነ ሌላውን የዓረብ ሀገራት ጥቅም ለመጉዳት ፍላጎት አሳይታ አታውቅም፤ ለወደፊትም ኢትዮጵያ ይህን አታደርግም። ኢትዮጵያም ከአረቡ ዓለም ጋር መልካም ግንኙነት መመስረት በመቻሏ የግብጽን የሃሰት ፕሮፓጋንዳ ከሽፏል። አሁንም ጠንክረን መስራት ይኖርብናል።
👉ኢትዮጵያ የያዘቺዉ አቋም ፍትሃዊ የዉሃ ሀብት አጠቃቀምን መሰረት ያደረገ በመሆኑ ምንም የሚያሰጋም ሆነ የሚያስፈራ ነገር የለም፡፡ እውነታ ላይ የተመሰረተ ዲፕሎማሲ መቼም ቢሆን ከስኬት ያደርሷል፤ ኢትዮጵያ እውነታን ይዛለች፤ እውነታን የያዘ ጊዜው ይገፋ እንደሆን እንጂ አሸናፊዎች ነን። ከግብጽ ውጭ ያሉት የተፋሰሱ ሀገራት የኢትዮጵያን አቋም ስለሚደግፉ፣ ግብፅ የያዘችው አቋም የትም አያደርሳትም፤ የሚበጀው ከኢትዮጵያ ጋር መተባበር ብቻ ነው፣ ጦርነት ዉስጥ ይገባሉ ብዬ አላስብም፡፡ እኛ ግን ከዲፕሎማሲው ጎን ለጎን ተባብረን በፍጥነት ግንባታዉን ማካሄድ ይኖርብናል።
👉እሳካሁኑ ባለው ሁኔታ ሱዳን ያላት አቋም በፍትሃዊነት ላይ የተመሰረተ ስለሆነ ልናደንቃት ይገባናል፡፡ ለወደፊትም የሚኖራት አቋም በእኛው አያያዝ ላይ የተመሰረተ ይሆናል፡፡ የግብፅ መንግስት ሴራ አሁንም ይቆማል ብዬ አላስብም፤ በመሆኑም እያንዳንዷን እንቅስቃሴ እየተከታተልን ማክሸፍ ይኖርብናል፤ የኢትዮጵያንና የሱዳንን የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት ይበልጥ ማሳደግ መልካም ግንኙነቶችን ማጠናከር ይኖርብናል።
ምንጭ በሪሳ ጋዜጣ ሰኔ 13 ቀን 2012 ዓ.ም