(ኢሳት) ዊሊያም ዳቪሰን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊትን ስም የሚያጠፋ ጥናት ለመስራት ከፍተኛ ገንዘብ መቀበሉ ተሰማ
የኢንተርናሽናል ክራይስስ ግሩፕ የኢትዮጵያ ወኪል ተመራማሪ የነበረው ዊሊያም ዳቪሰን የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊትን ስም የሚያጠፋ ጥናት ለመስራት ከአሜሪካው ስቴት ዲፓርትመንት ከፍተኛ ገንዘብ ተመድቦለት እየተንቀሳቀሰ መሆኑ ተሰማ፡፡
የኢሳት የደህንነት የመረጃ ምንጮች እንደጠቆሙት ዊሊያም ዳቪሰን ከኢትዮጵያ መባረሩን ተከትሎ ቢሮውን በናይሮቢ በማድረግ ለህወሓት እየሰራ መሆኑን የመረጃ ምንጮቻችን ገልፀዋል፡፡
ባለሙያው በአሁኑ ወቅት ከአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንት ከፍተኛ ገንዘብ ተመድቦለት የኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊትን ስም የሚያጠፋ ጥናት ለመስራት እየተንቀሳቀሰ መሆኑ ተሰምቷል፡፡
ዊሊያም ዳቪሰን ኢትዮጵያ ውስጥ ገብቶ ጥናቱን መስራት ስለማይችል በኢትዮጵያ የምትገኘውን የኢንተርናሽናል ክራይስስ ግሩፕ አባል የሆነችውን ዝምባቡዌያዊት ባለሙያ አብራው እንድትሰራ ቢያግባባትም ልትቀበለው እንዳልቻለችም ተገልጧል፡፡
ዝምባቡዌያዊት ባለሙያ እንደዚህ ባለ ህገወጥ ተግባር አልሳተፍም፣ ብዙ ዋጋ ያስከፍለኛል፣ እዚህ ጉዳይ ውስጥ መግባት አልፈልግም በማለት በመቃወም ስራወን እንደለቀቀችም ምንጮቻችን ገልፀዋል፡፡
የአሜሪካ ስቴት ዲፓርትመንት በዚሁ በናይሮቢ የትግራይ ምላሽ ሰጪ ቡድን በማቋቋም እየሰራ መሆኑንም ምንጮቻችን ጠቁመዋል፡፡
ቡድኑ በእርዳታ ስም የስለላ፣ የመረጃ ልውውጥ ስራዎችን በመስራት የህወሓት ታጣቂ ቡድንን ለመደገፍ የተቋቋመ መሆኑንም ምንጮቻችን አክለዋል፡፡