አፋን ኦሮሞ ቋንቋን የማይችሉ እና የተወሰኑት ብቻ አማርኛ ቋንቋ የሚችሉ የኤርትራ ወታደሮች በደቡብ ኦሮሚያ ውስጥ አሉ ስለሚባለው ጉዳይ መረጃ የለም – ውጭ ጉዳይ

ዛሬ ሳምታዊ መግለጫ የሰጡት የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃለ አቀባይ አማባሳደር ዲና ሙፍቲ “የኤርትራ ወታደሮች በምእራብ ኦሮሚያ ውስጥ በሚገኙ ዞኖች እና በደቡብ ኦሮሚያ ውስጥ አሉ” ስለሚባለው ጉዳይ ተጠይቀው ነበር።

አምባሳደር ዲና “መረጃ የለኝም” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።

የኦሮሞ ነጻነት ግንባር (ኦነግ) ፥ የኤርትራ ወታደሮች በኦሮሚያ ክልል በተለይ በቦረና ዞን ነጌሌ ከተማ አካባቢ እንዲሁም በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ዞን አባይ ጮመን በሚባል ስፍራ መታየታቸውን ገልፆ ነበር።

ኦነግ የኤርትራ ወታደሮች ናቸው ያላቸው ግለሰቦች “ሁሉም አፋን ኦሮሞ ቋንቋን የማይችሉ እና የተወሰኑት ብቻ አማርኛ ቋንቋ የሚችሉ ናቸው” ብሏል።

አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ፥ “የኤርትራ ወታደሮች በኦሮሚያ ክልል ውስጥ ታይተዋል ስለመባሉ ምንም መረጃ የለኝም” ብለዋል።

በትግራይ ክልል ያሉት የኤርትራ ወታደሮችን በተመለከተም ተጠይቀው ምላሽ ሰጥተዌ።

አማባሳደር ዲና የኤርትራ ወታደሮች ከትግራይ ክልል መውጣት መጀመራቸውን ገልጸው ፣ ይህንንም መከላከያ ሚኒስቴር ማረጋገጡን አስታውሰዋል።

ትግራይ ክልል ከሚገኙ የኤርትራ ወታደሮች ምን ያክሉ ወጡ? መቼ ሙሉ በሙሉ ይወጣሉ ? የሚለውን በተመለከተ “ሙሉ መረጃ የለኝም” ሲሉ መልሰዋል።

በሌላ በኩል የሰሜን አትላንቲክ ቃልኪዳን ጦር (NATO) በትግራይ ካለው ችግር ጋር በተያያዘ “ኢትዮጵያን ለመውረር ተዘጋጅቷል” እየተባለ ስለሚወራው ጉዳይ ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ መረጃ እንደሌለው ጠቁመዋል።

አምባሳደር ዲና ፥ “ኢትዮጵያ ከሁሉም የኔቶ (NATO) አባላት ጋር መልካም ግንኙነት ነው ያላት፤ ይህንን ያደርጋሉ የሚል እምነት የለኝም” ሲሉ የግል አስተያየት ሰጥተዋል።

የዚህ ዘገባ ባለቤት “አል ዓይን ኒውስ” ነው።