የትግራይ ተወላጅ የሆኑ የሰራዊት አባላት ወደ ሀገራችን አንሄድም በማለት ጁባ አየር ማረፊያ ላይ በመንከባለልና በመጮህ ሁከት ለመፍጠር ሞክረዋል – የሀገር መከላከያ ሰራዊት

ከደቡብ ሱዳን ጁባ ወደ ኢትዮጵያ አዲስ አበባ አንመለስም ያሉ የኢትዮጵያ ወታደሮችን በሚመለከት የመከላከያ ኢንዶክትሪኔሽን ዋና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ሜ/ጄ መሃመድ ተሰማ ምላሽ ሰጥተዋል።

ሜጄር ጀነራል መሃመድ ፥ ከሰሞኑ የ15ኛ ሞተራይዝድ ሰላም አስከባሪ ሻለቃ በጁባ የሚገኘውን ቆይታውን ላጠናቀቀው ሰላም አስከባሪ ሀይል በመቀየር ላይ እንዳለ አስታውሰዋል።

በዚህ ሂደት የትግራይ ተወላጅ የሆኑ የሰራዊት አባላት ወደ ሀገራችን አንሄድም በማለት ጁባ አየር ማረፊያ ላይ በመንከባለልና በመጮህ ሁከት ለመፍጠር ሞክረዋል ብለዋል።

ይህን ድርጊት የፈፀሙትንም የህወሓት ተላላኪዎችና ቅጥረኞች ሲሉ ነው የጠሯቸው።

የሰራዊት አባላቱ የሰራዊቱን እና የሀገሪቱን መልካም ስምና ዝና ለማጠልሸት ፣ በዩኤን የተለያዩ ቦታዎች ተቀጥረው የሚሰሩ የትግራይ ተወላጆች UNHCR የተባለውን ግብረ ሰናይ ድርጅት የሚዲያ ሽፋን እንዲያገኝ በማመቻቸት ጉዳዩን አለም አቀፍ ማህበረሰብ እንዲሰማው ለማደረግ ተሞክሯል ሲሉ አብራርተዋል።

UNHCRም ለአለም አቀፉ ማህበረሰብ ያስተጋባው ዘገባ ያልተገባ መሆኑን በመግለፅ ይቅርታ ሊጠይቅ እንደሚገባ ሜ/ጄ መሀመድ ተሰማ ተናግረዋል፡፡

አሁን ላይ መከላከያ የቀሩ የህወሓት አባላትን አድኖ ለመያዝ በከፍተኛ ሞራልና ወኔ እየሰራ ነው በዚህም በግለሰቦች እንዲህ አይነት ድርጊት መፈፀሙ ሰራዊቱን የማይወክልና የግለሰቦች ብቻ እንደሆነ ሊታወቅ ይገባል ሲሉ ሜ/ጄነራል መሀመድ ተናግረዋል።

በጁባ ድርጊቱን የፈፀሙ የትግራይ ተወላጅ የሰራዊት አባላቱ ሌሎች ትግራይ ተወላጆችን የማይወክሉ እንደሆኑና ፣ አሳፋሪ ተግባር የፈፀሙ ናቸው ሲሉም ገልፀዋል።

ሜ/ጄነራል መሀመድ ፥ “ይህንን ተግባር እንደ ትልቅ ነገር እያራገቡ የሚገኙ የሚዲያ አውታሮችና ተከፋይ አምደኞችም ድርጊቱን በተገቢው በመረዳት ሚዛናዊነትን በመጠቀም ሊዘግቡት ይገባል” ብለዋል።

(ከኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት)