ጃዋር መሐመድ የታዋቂ ሰዎችን ስልክ በመጥለፍ ሚስጥራዊ ጉዳዮችን ሲያዳምጥ ነበር ሲል ፖሊስ ገለጸ

አቶ ጃዋር መሃመድ በግለሰብ እጅ የማይገኙ ሳተላይቶችና ከውጭ በድብቅ የገቡ ኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች አማካኝነት የታዋቂ ሰዎችን ስልክ በመጥለፍ ሚስጥራዊ ጉዳዮችን ሲያዳምጡ እንደነበር ፖሊስ ገለጸ ፡፡
መርማሪ ፖሊስ በአቶ ጃዋር መሃመድ ቤት በግለሰብ እጅ የማይገኙ ሳተላይቶችና ከውጭ በድብቅ የገቡ ኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች ማግኘቱን ገለጸ
(ኤፍ ቢ ሲ) የፌደራል መርማሪ ፖሊስ በአቶ ጃዋር መሃመድ ቤት በድጋሚ ባደረገው ፍተሻ በግለሰብ እጅ የማይገኙ ሳተላይቶችና ከውጭ በድብቅ የገቡ ኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎች ማግኘቱን ገለጸ።
አቶ ጃዋር መሃመድ በዛሬው እለት በፌደራሉ የመጀመሪያ ደረጃ ፍርድ ቤት አራዳ ምድብ ተረኛ ችሎት ልደታ አዳራሽ ቀርበዋል፡፡
መርማሪ ፖሊስም ባለፉት ቀናት ያከናወናቸውን ስራዎች በጠቀሰበት ሪፖርቱ በአቶ ጃዋር መኖሪያ ቤት በድጋሚ ባደረገው ፍተሻ መሳሪያዎቹን ማግኘቱን አስታውቋል፡፡
በመሳሪያው አማካኝነትም የታዋቂ ሰዎችን ስልክ በመጥለፍ ሚስጥራዊ ጉዳዮችን ሲያዳምጡ እንደነበር ማስረጃ መሰብሰቡን አስታውቋል፡፡
ከዚህ ባለፈም በርካታ ተጨማሪ አዳዲስ ግኝቶችን በምርመራ ማግኘቱን ለችሎቱ ይፋ አድርጓል።
አቶ ጃዋር በበኩላቸው የፖሊስ ምርመራ እኔን አይመለከትም ይህ የፖለቲካ ጉዳይ ነው ሲሉ ተቃውሞ አሰምተዋል።
ፍርድ ቤቱም አቶ ጃዋር ባነሷቸው አቤቱታዎች ዙሪያ ትዕዛዝ ሰጥቷል፡፡