የኦሮሞ ብሄረተኞች ጥያቄ የእኩልነት ሳይሆን የበላይነት ነው #ግርማካሳ

(በወለጋ በሚደረጉ ጥሮነቶች የተፈናቀሉ እናት)

የኦሮሞነት ፖለቲካን ተቃውመን ስለኦሮሞ ማህበረሰብ ስንጽፍ ነፍጠኛ  ጸረ_ኦሮሞ ይሉናል፡፡ ኦሮሞነትን እነርሱ ጋር ብቻ እንዳለ በማሰብ እነርሱ የኦሮሞ ተሟጋች ሌላው የኦሮሞ ጠላት አድርገው ያስባሉ፡፡ እውነታው ግን ኦሮሞ የሌለበት ኢትዮጵያዊ በጣም ጥቂት ነው፡፡ እኔ አዲስ አበባ ተወልጂ ያደኩ ነኝ፡፡ ሁለት አያቶቼ ኦሮሞ ናቸው፡፡ ከቦረናና ከአዳ፡፡ የኦሮሞ ማህበረሰብ የሚደርስበት መከራ እንደ ኢትዮጵያዊ ያመኛል፡፡ አሁን ኦሮሞን እንወክላለን የሚሉ ጥቂት ጽንፈኞች ከማንም በላይ እየጎዱ ያሉት ኦሮሞዉን ነው ብዮ ነው አጥብቄ የምቃወማቸው፡፡

በማህበራዊ ሜዲያ ጉልህ ተሳትፎ ከሚያደርጉ የኦሮሞ ብሄረተኛና አፍቃሪ ኦህዴድ ጦማሪ መካከል አንዱ ዶ/ር ደረጄ ገረፋ ቱሉ ነው። ዶ/ር ደረጄ፣ የኦሮሞ ጥያቄን አልመለሰም በሚል ዶ/ር አብይ አህመድ ላይ ቅሬታዉን ያሰማል፡፡ “ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ስልጣን ሲመጡ መሬት የረገጡ እና ለረጅም ዓመት ህዝቡ ሲታገልላቸው ያሉ የኦሮሞ ጥያቄዎች ነበሩ።ከነዚህ መካከል የሸገር እና የአፋን ኦሮሞ ጉዳይ ዋና ዋናዎቹ ናቸው። በተለይ የሸገር ጉዳይ ለህወሃት ከስልጣን ማማ መፈጥፈጥ ዋናው እና የቅርብ ገፊ ምክንያት ነው” ሲል ነበር ቅሬታዉን ያቀረበው፡፡ዶ/ር ደረጄ ብቸውን አይደለም፡፡ አብዛኞቹ የኦሮሞ ብሄረተኛ ፖለቲከኞችና አክቲቪስቶች “የኦሮሞ ጥያቄዎች” አልተመለሱም በሚል ጠቅላይ ሚኒስትሩን እንደ “ከሃዲ” በመቁጠር ማርጎምጎም ከጀመሩ በጣም ሰነባብተዋል፡፡

ከዶ/ር ደረጄ አስተያየት እንዳየነው፣ እነዚህ የኦሮሞ ብሄረተኞች የ”ኦሮሞ ሕዝብ ጥያቄ አልተከበረም” ሲሉ አንዱ የሚያነሱት የኦሮሞ ባህል፣ ቋንቋ አልተስፋፋም የሚል ነው፡፡ እስቲ ይሄን ቅሬታቸው ምን ያህል ሚዛናዊ እንደሆነ እንፈትሸው፡

  • በአዲስ አበባ ፣ ስታዲየም ፊት ለፊት፣ ብዙ ፎቆችን የያዘ የኦሮሞ ባህል መዓከል አለ፡፡ በዚህ ባህል ማእክል የኦሮሞን ባህልና ስርዓት የሚገልጹ የተለያዩ ኤግዚቢሽኖች ፣ ስብሰባዎች፣ ሴሚናሮች …ይደረጋሉ፡፡
  • ለሁለት ቀናት የከተማዋን ዋና ዋና መንገዶች በመዝጋት፣ ሌላው ማህበረሰብ ቤቱ እንዲቀመጥ ተደርጎ፣ ኢሬቻን በአዲስ አበባ ያለ ምንም ችግር ተከብሯል፡፡
  • በኦሮሞ ክልል መንግስት ባጀት በኦሮምኛ(በላቲን) የሚያስተምሩ አራት ትምህርት ቤቶች እንዲከፈቱ ተደርጓል፡፡ የአዲስ አበባ መስተዳደር መሬት ሰጥቶ፣ ትምህርት ቤቶች ከሁለት አመታት በፊት ተገንብተው በኦሮምኛ ትምህርት እየሰጡ ነው፡፡ እነዚህ፣  የኦሮሞ ክልል በአሻጥር፣ በኔ ባጀት ነው ብሎ የከፈታቸውን ት/ቤቶች አሁን በአዲስ አበባ መስተዳደር ባጀት እንዲንቀሳቀሱ እየተደረገ ነው፡፡ ያ ብቻ አይደለም፡፡ ከ120 በላይ ሌሎች ትምህርት ቤቶች፣ኦሮምኛ እየተሰጠ ነው፡፡
    በአዲስ አበባ ብቻ አይደለም፡፡ ከተፈለገም በባህር ዳር፣ በጂጂጋ፣ በመቀሌ ..የኦሮሞና ባህልና ቅርስ የሚያስተዋወቁ ማእከላትን፣ በኦሮምኛ የሚያስተምሩ ት/ቤቶች ቢከፍቱ፣ ኢሬቻን ሆነ ሌላ ማንኛውን የኦሮሞ በዓላትን እናክብር ቢሉ የሚቃወማቸው ይኖራል ብዬ አላስብም፡፡፡ በአሁኑ ወቅት ኦሮሞዎች ባህላቸውን ቋንቋቸውን በማስፋፍት ረገድ ምንም አይነት መሰናክል የለባቸውም፡፡ ለማስታወስ ያህል እንደውም፣ ከአንድ አመት በፊት የቀድሞ የአማራ ክልል ረእሰ መስተዳደር አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በባህር ዳር የኦሮሞ ባህል ማእከል ግንባታ መሬት ለመስጠት ፍቃደኛ እንደነበሩም ተገልጾ ነበር፡፡

ሌላው የኦሮሞ ብሄረተኞች ፣ የ”ኦሮሞ ሕዝብ” ጥያቄ አልተከበረም” የሚያስብላቸው ሌላው ነጥብ ኦሮምኛ የፌዴራል ቋንቋ ለምን አልሆነም የሚለው ነው፡፡ የዶ/ር አብይ አስተዳደር ኦሮምኛ ብቻ ሳይሆን ትግሪኛ፣ ሶማሌኛ፣ አፋርኛና ሌሎችም ከአማርኛ ጋር የፌዴራል የስራ ቋንቋ ለማድረግ እቅድ እንዳለው ገልጿል፡፡ያ ማለት ጥያቄውን ተግባራዊ ለማድረግ እየተሰራ፣ በአጭሩ ጥያቄው እየተመለሰ ነው ማለት ነው፡፡

የኦሮሞ ብሄረተኞች በርግጥ የዶ/ር አብይ አስተዳደር ኦሮምኛን የፌዴራል ቋንቋ ለማድረግ እየሰራ መሆኑ ያውቃሉ፡፡ ግን ከምንም ነገር በላይ ያበሳጫቸው የሚመስለኝ፣ ትግሪኛ፣ ሶማሌኛና፣ አፋርኛም  መካተታቸው ነው፡፡ ሐሳባቸው የነበረው ኦሮምኛና አማርኛ ብቻ የፌዴራል የስራ ቋንቋዎች ሆነው፣ በፌዴራል መንግስት መስሪያ ቤቶች “ኦሮምኛም ማወቅ ያስፈለጋል” በሚል ኦሮምኛ ተናጋሪው ብቻ በስፋት የስራ እንድል እንዲያገኝ ማድረግ ነበር፡፡ ብርሃነ መስቀል የሚባለው፣ በሎስ አንጀለስ የኢትዮጵያ ቆንስል ጽ/ቤት አምባሳደር ሆኖ የሚሰራው፣  ኦሮምኛ የፌዴራል ቋንቋ ከሆነ፣ የፌዴራል ከተማ አዲስ አበባ ከንቲባና የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስተር ኦሮምኛ የሚናገሩ መሆን አለባቸው እንዳለው ማለት ነው፡፡

ትግሪኛ፣ ሶማሌኛ …ከተጨመሩ ግን ያ ሊሆን አይችልም፡፡ የፌዴራል የስራ ቋንቋ መሆን፣ ልክ እንደ ደቡብ አፍሪካ፣ በዋናነት ቋንቋዉን የሚናገሩ ዜጎች ባሉባት አካባቢ የፌዴራል መንግስት አገልግሎት ማግኘት ላይ ያተኮረ ይሆናል፡፡

እዉነቱ ይሄ ሆኖ እያለ ፣ የኦሮሞ ብሄረተኞች ፣ የዶ/ር አብይን አስተዳደር በዚህ ረገድ የኦሮሞን ጥቅም አላስጠበቀም ብለው የሚከሱት ዉህ የሚቋጥር አይደለም፡፡ የኦሮሞ ጥያቄ ስላልተመሰለሰ አይደለም፡፡ ጥያቄው ተመልሷል፡፡ ግን አላማቸው የኦሮሞን ባህል ማስፋፋት፣ ኦሮምኛ ተደራሽነቱን ማስፋት ሳይሆን፣ የሌሎች ማህበረሰብትን ባህል መጨፍለቅ፣ ሌሎች ቋንቋዎች እንዳይነገሩ ማድረግ ስለሆነ ፣ የፈለገ የኦሮሞ ባህል የሚያንጸባርቁ ስራዎች ቢሰሩም አያረካቸውም፡፡ ኦሮምኛ ለምን አይነርም ሳይሆን፣ ከኦሮምኛ ውጭ ሌላ ቋንቋ ለምን ይነግራል ነው ጥያቄያቸው፡፡ኦሮሞ ለምን እኩል አይሆንም ሳይሆን ኦሮሞ ለምን ልዩ ጥቅም አያገኝም፣ ለምን የበላይ አይሆንም ነው አጀንዳቸው፡፡

በቋንቋና በባህል ረገድ የኦሮሞ ማህበረሰብ ጥያቄ ተመልሷል፤ እየተመለሰም ነው፡፡ ከላይ እንዳልኩት ችግሩ ያለው፣ የኦሮሞ መሬት በሚሉት አካባቢ (አሁን ኦሮሚያ የሚባለው፣ አዲስ አበባ፣ ወሎ፣ ድሬዳዋ፣ ሞያሌን ጨምሮ) ከኦሮምኛ፣ ከገዳ ከመሳሰሉ የኦሮሞ ባህሎች ውጭ ሌላ ነገር ማየት አለመፈለጋቸው ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ምንም ማሽሞንሞን የማያስፈለገው ዘረኝነትና ጥላቻ ነው፡፡

በኔ እይታ እነ ዶ/ር ደረጄ ባቀረቡበት ምልኩ ሳይሆን በሌላ ጎኑ ገዢው ፓርቲ ኦህዴድ የኦሮሞ ማህበረሰብ ክፉኝዐ በድሏል ብዬ እከራከራለለሁ፡፡

የኦሮሞ ማህበረሰብ ዋና ጥያቄዎች የልማት፣ የሰላም፣ የዴሞክራሲና የእኩልነት ጥያቄዎች ናቸው፡፡ የስራ አጥነት ተወግዶ የኦሮሞ ልጆች የስራ እድል አግኝተው ኑሯቸውን እንዲያሻሽሉና ከተስፋ መቁረጥ ነጻ እንዲወጡ ነው፡፡

የኦህዴድ ገዢዎች እነዚህን መሰረታዊ የሕዝቡን ጥያቄዎች አልመለሱም፡፡ በኦሮሞ ክልል በቦረና፣ ጉጂና ወለጋ ጦርነት ነው ያለው፡፡ በአርሲ፣ ባሌና ሃረርጌ በመሳሰሉት ቦታዎች ደግሞ ቄሮ የሚባለው አሸባሪ ቡድን እያሸበረ ነው፡፡ በቅርቡ፣ ጃዋር መሐመድ ባደረገው ጥሪ፣ በዚያ የተፈጸሙ፣ ሩዋንዳ ከተደረገው የባሰ አሰቃቂ የጭካኔ ተግባራትን ሁላችንም የምናስታወሰው ነው፡፡ ህግ የበላይ ስላልሆነ ፣ በክልሉ አናርኪ ስለበዛ፣ ማንም ጉልበተኛ መንግስት ነኝ ብሎ የፈለገውን ስለሚያደርግ፣ የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም እንቅስቃሴዎች እየሞቱ ነው፡፡ የኦሮሞ ልጆች አማርኛ በሚገባ እንዳይማሩ ተደርገው በሌሎች የአገሪቷ አካባቢዎች ስራ የማግኘት እድላቸው የጨለመ ሆኗል፡፡ ይሄ ሁሉ አልበቃ ብሎ የኦሮሞ ማህበረሰብ በሌሎች ማህበረሰባት እንዲጠላ፣ መቃቃር እንዲጨምርና ሕዝቡ በዘላቂነት ከሌሎች ጋር በሰላም እንዲኖር የሚያደርገውን ታሪካዊ ትስስር ኦህዴዶችና የኦሮሞ ፖለቲከኞች እያላሉት ነው፡፡ የኦሮሞ ፖለቲከኞችና የፖለቲካ ነጋዴዎች በሚያራመዱት ዘረኛ የኦሮሞነት ፖለቲካና ማህበረሰቡ ከጌዴዎ፣ ከሃረሬ፣ ከሶማሌ፣ ከጉሙዝ፣ ከአማራ፣ ከአዲስ አበቤው …..ከሁሉም ጋር እንዲጋጭ እየተደረገ ነው፡፡

ለዚህ ነው ኦህዴድ/ኦዴፓ እንዲሆን የኦሮሞ ድርጅቶች፣  የኦሮሞ ማህበረሰብን በዘላቂነት የሚጠቅም፣ የህዝቡን መሰረታዊ ጥያቄዎች የሚመለስ ስራ እየሰሩ ሳይሆን ኦሮሞውን ትልቅ የማህበራዊ፣ የፖለቲካዊና የኢኮኖሚያዊ አዘቅት ውስጥ እየዘፈቁት ነው የምንለው፡፡