በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን እስረኞች የረሐብ አድማ ጀመሩ

DW – በታንዛኒያ እስር ቤቶች የሚገኙ በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን የረሐብ አድማ መጀመራቸውን በታንዛኒያ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሚንስትር ካውንስለር አቶ ቴዎድሮስ ግርማ ተናገሩ።

ኢትዮጵያውያኑ የረሐብ አድማ ያደረጉትም «እስካሁን ድረስ ወደ ኢትዮጵያ መመለስ አልቻልንም በሚል በመሰላቸት እና ተስፋ በመቁረጥ ነው» ብለዋል። ኤምባሲው ከታሳሪዎቹ ጋር በመነጋገር የኢትዮጵያ ኤምባሲ እስከ ባለፈው ግንቦት በአገሪቱ እስር ቤቶች ባደረገው አሰሳ ያስፈታቸውን 1050 ሰዎች ወደ ኢትዮጵያ መመለሱን አቶ ቴዎድሮስ ገልጠዋል።

ባለፈው ሐሙስ የረሐብ አድማ ከጀመሩ መካከል 17 ኢትዮጵያውያን ተዳክመው አርብ ዕለት ወደ ሕክምና ማዕከላት ተወስደው እንደነበር ጉዳዩን በቅርበት የሚከታታተሉ አንድ ግለሰብ ለዶይቼ ቬለ ተናግረዋል።

ግለሰቡ ምግብ ባለመመገባቸው የተዳከሙት ኢትዮጵያውያን እገዛ ከተደረገላቸው በኋላ ወደ እስር ቤት መመለሳቸውንም ገልጸዋል። ለዶይቼ ቬለ በደረሰው መረጃ መሰረት ምቤያ፣ ማወይኒ፣ ኪጎንጎኒ፣ ኪቢቲ እና ኪባሃ በተባሉ የታንዛኒያ እስር ቤቶች የሚገኙ ከ500 በላይ ኢትዮጵያውያን በተለያየ ወቅት የረሐብ አድማ አድርገዋል።