
የፎቶው ባለመብት, SM
የምስሉ መግለጫ, ጥቃት የተፈፀመበት ሳንቃ ጤና ጣቢያ ከፊል ገጽታ
በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ጉባላፍቶ ወረዳ ቅዳሜ መስከረም 17/2018 ዓ.ም. ጤና ጣቢያ ላይ በተፈፀመ የድሮን ጥቃት ነፍሰ ጡር እናትን ጨምሮ የአራት “ሰላማዊ ሰዎች” ሕይወት ሲያልፍ 10 በላይ ሰዎች ደግሞ መቁሰላቸውን የዓይን እማኞች እና የሕክምና ምንጮች ለቢቢሲ ተናገሩ።
ጥቃቱ ከዞኑ እና ከወረዳው ዋና ከተማ ወልዲያ 20 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ሳንቃ በተባለች የክላስተር ከተማ በሚገኝ ጤና ጣቢያ ላይ ከቀኑ 06፡00 አካባቢ መፈፀሙን አራት የዓይን እማኞች እና የአካባቢው ነዋሪዎች ተናግረዋል።
የዞኑ አስተዳደር ስለጥቃቱ እና ስለደረሰው ጉዳት ለመናገር እንደማይችል ለቢቢሲ ተናግሯል።
በስፍራው የነበሩ የጤና ጣቢያው አንድ ባለሙያ መሣሪያው በዋናነት ፊት ለፊት በሆነው እና ታካሚዎች ተኝተው በሚታከሙበት “5 ቁጥር” በተባለው ክፍል ላይ ማረፉን ተናግረዋል።
ከጥቃቱ እንደተረፉ የተናገሩት የጤና ጣቢያው ባልደረባ ጥቃቱ የደረሰበትን ቅፅበት ሲገልፁ “ምንም ራሴን አላውቅም፤ መሬት ተሰንጥቆ የዋጠን ነው የመሰለን። ከጎኔ የነበሩት ሲወድቁ እኔን እግዚአብሔር ነው የከለለኝ” ሲሉ እማኝነታቸውን ሰጥተዋል።
ፍንዳታውን ሰምተው በፍጥነት አካባቢው ላይ መድረሳቸውን የተናገሩ ሌላ የዓይን እማኝ ጤና ጣቢያው ውስጥ የነበረ የቤተሰብ አባላቸው ከጥቃቱ መትረፉን ገልፀው፤ ዘግናኝ ሁኔታ መመልከታቸውን ለቢቢሲ ተናግረዋል።
ወከባ እና ተጨማሪ የጥቃት ስጋት በመፈጠሩ “በደመ-ነፍስ . . .የደማውም፤ የተመታውም እየተዛዘለ ነው የወጣው” ሲሉ ክስተቱን ተናግረዋል።
የቆሰሉ ሰዎችን ማውጣታቸውን እና አስከሬን ማንሳታቸውን የተናገሩ ሌላ የዓይን እማኝ ደግሞ ለመግለፅ የሚከብድ ሁነት ማየታቸውን ተናግረዋል።
“ፍንጣሪው