የሜቲክ አሻጥር እና የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ሃዲድ የማንጠፍ ስራ

ባቡር ወዲያ ማዶ ሃዲድ ወዲህ ማዶ

የአዲስ አበባ ቀላል ባቡር ሃዲድ የማንጠፍ ስራ ወደመጠናቀቁ በተቃረበበት ሰአት ላይ ሜቴክና የምድር ባቡር ድርጅት ሃይለኛ ውዝግብ ውስጥ ገቡ ።
የውዝግቡ መነሻ ሜቴክ ለአዲስ አበባ ቀላል ባቡር የሚሆኑ ሰው ማጓጓዣ ፉርጎዎችን ማምረት ያለብኝ እኔ ነኝ አለ ። ምድር ባቡር ደግሞ እነዚህ ሰው ማጓጓዣ የከተማ ባቡሮች ኢንተርናሽናል ደረጃቸውን የጠበቁና የሰው ማመላለሻ ፉርጎዎችን በመስራት ልምድ ባለው ድርጅት ነው መሰራት ያለበት ። ስለዚህ እነዚህን ፉርጎዎች አለም አቀፍ እውቅና ካለው የቻይና ኩባንያ አዝዣለሁ በሚል የተነሳ ውዝግብ ነበር ። አለመግባባቱ እየጠነከረ መጣና ሜቴክና ምድር ባቡር ድርድር ተቀመጡ ። ከዛም ሜቴክ ለናሙና የሚሆኑ የተወሰኑ የህዝብ ማመላለሻ ፉርጎዎችን ሰርቶ እንዲያቀርብ ። ከቻይና የታዘዙትም ፉርጎዎች እንዲገቡ ስምምነት ተደረሰ ።
ለሜቴክ የተወሰነ ብር ተገባለት እዚህ አዲስ አበባ ሜክሲኮ አደባባይ በሚገኘው የብረታ ብረትና ኢንጂነሪንግ ወርክ ሾፕ ፡
ብረት እየተቆረጠ ላሜራ እየተሰነጠቀ ዘመናዊ ህዝብ ማመላለሻ የባቡር ፉርጎ ለመስራት ስራ ተጀመረ ።
• ልብ በሉ ሜቴክ ከዚህ በፊት አንድም የባቡር ፉርጎ ሰርቶ አያውቅም ።
• በዚህ መስክ የተሰማራም ሰራተኛ አላሰለጠነም ።
እናስ ? …… እናማ በገገማ ለአዲስ አበባ ቀላል ባቡር የሚሆኑ ተጎታች ባቡሮች ለማምረት የተጀመረው ስራ ተጠናቆ የመጀመሪያዎቹ ፉርጎዎች ሜክሲኮ ከሚገኘው ወርክ ሾፕ ተጭነው ወደ ምድር ባቡር ግቢ ሄደው በረዥሙ ሃዲድ ላይ ተገጥመው ሙከራ ሊደረግባቸው ዝግጁ ሆኑ ………….. አሁን የቀረው ባቡሮቹን ሃዲዱ ላይ ማስቀመጥ ነውና ስራ ተጀመረ ። ቢባል ቢባል የባቡር ፉርጎዎቹ የብረት ጎማ ከሃዲዱ ጋር እንዴት ይግጠም …….. የተሰራው ፉርጎ ስፋትና የሃዲዱ ስፋት ፈፅሞ አይገናኝም ።
ሜቴክ ቀላል ባቡሮቹን እንደመኪና አስቦ ያለሃዲድ ሊያስኬዳቸው ፈልጎ ይሁን .. ምን ይሁን አልታወቀም ብቻ ሃዲድ እዛ ፉርጎ እዚ ሆነና አረፈው ። የባቡር ሃዲድም ሆነ የተጎታች ፉርጎዎች ስፋት ማንም እንደፈለገው የሚያጠበውና የሚያሰፋው ሳይሆን በአለም አቀፍ ደረጃ በተዘጋጀ ወጥ የሆነ ስታንዳርድ የሚሰራ በመሆኑ ሜቴክ እንደዚህ አይነት ይደረጋል ተብሎ የማይታሰብ ስህተት መስራቱ በጉዳዩ ዙሪያ በነበሩ ሰራተኞች ከፍተኛ ግርምትን ፈጠረ ።
በፉርጎዎቹ ላይ የነበረው ሌላው መሰረታዊ ችግር ይሄ ብቻ አልነበረም ። እንደው እድል ቀንቶት ፉርጎዎቹና ሃዲዱ ተገጣጥመውለት ቢሆንም ኖሮ ባቡሮቹ ግልጋሎት መስጠት አይችሉም ነበር ምክንያቱም ዛሬ ከተማችን ውስጥ ያሉት የባቡር ፉርጎዎች እንደምናያቸው በግራና በቀኝ ግድግዳቸው ላይ ሁለት አውቶማቲክ በር የተገጠመላቸው ሲሆኑ ሜቴክ ፉርጎዎቹን እንደ አውቶቡስ አስቧቸው ነው መሰል በር ሰርቶ ያመጣው በአንድ በኩል ብቻ ነበር በነዚህ መሰረታዊ ችግሮች ምክንያት ሜቴክ ለፉርጎዎቹ መስሪያ የወሰደው ብር ባክኖ ዛሬ የምናያቸው የከተማ የባቡር ፉርጎዎች ሙሉ ለሙሉ ከቻይና መጡ ። የሜቴክ እየሰራን እንማራለን ፡ እየተማርን እንሰራለን መርህ ያልገባበት ቦታ አልነበረም ።