በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ትኩረቱን ያደረገ የፓናል ውይይት እየተካሄደ ነው

Image may contain: 2 people, people sitting and indoor

(ኤፍ ቢ ሲ) በሀገሪቱ እና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ያተኮረ የፓናል ውይይት እየተካሄደ ነው።

የውይይት መድረኩ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የስብከተ ወንጌል እና ሃዋርያ ተልዕኮ መምሪያ አስተባባሪነት የተዘጋጀ ነው።

በፓናል ውይይቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ ሊቃውንት እና ምሁራን ተሳትፈዋል።

የፓናል ውይይቱ “በጎውን ማን ያሳየናል?” በሚል መሪ ቃል ነው እየተካሄደ የሚገኘው።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ብጽዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፥ በአሁኑ ወቅት በሀገሪቱ አንዳንድ አካባቢዎች እየተከሰቱ ያሉ ችግሮችን ማረም፣ መፍታትና ማስተካከል አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል።

ሰላም ከሌለ ልማትና እድገት አይኖርም ያሉት ብፁዕነታቸው፥ የሀገሪቱን ሰላም፣ አንድነት እና ፍቅር ለማስጠበቅ ሁሉም የበኩሉን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል።

አባቶቻችን ሀገርን ከጠላት ጠብቀው ለኛ አስረክበዋል፤ የአሁኑ ዘመን ትውልድም ሰላም፣ ፍቅርና መከባበርን ለተተኪው ትውልድ የማስተላለፍ ሃላፊነት አለበት ብለዋል።Image may contain: 1 person, sitting, crowd and indoor

በአሁኑ ወቅት ትርክት የርዕዮተ ዓለም ማጠንጠኛ እና የፖለቲካ መስበኪያ መሳሪያ መሆኑን ጠቅሰው፥ ይህ አካሄድ አዲሱን ትውልድ እያለያየ እንደሚገኝው አንስተዋል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ጠቅላይ ጽህፈት ቤት ሃላፊ ብፁዕ አቡነ ያሬድ በበኩላቸው፥ በአሁኑ ወቅት የሚስተዋሉ መሰል ችግሮችን በጥናት በመታገዝ መፍታት እንደሚገባ ጠቁመዋል።

ቤተክርስቲያን የሌሎችን የእምነት ነጻነት እንደምታከብር ሁሉ እርሷም ልትከበር እንደሚገባትም አጽንኦት ሰጥተዋል።