የ“አድገናል አላደግንም፤ ለምተናል አለማን፤” ስሜታዊ ትርጉም
ጌታቸው አስፋው
(የብሔራዊ ኢኮኖሚ ዕቅድ ባለሙያ)
ስለ አብዛኛው ሰው የኑሮ ዓይነትና ደረጃ አንዳንድ ሰዎች ሲገልጹ ኑሮ ተሻሽሏል ብለው ይናገራሉ፤ ይጽፋሉ፡፡ አንዳንድ ሰዎችም ይሰማሉ፤ አይናገሩም፡፡ ያነባሉ፤ አይጽፉም፡፡ የማይናገሩ የማይሰሙ፤ የማይጽፉና የማያነቡም ብዙ ሰዎች አሉ፡፡ ቁጥራቸውም ቀላል አይደለም፡፡ ከሚናገሩት ከሚሰሙት፤ ከሚጽፉትና ከሚያነቡትም በእጅጉ ይበልጣል፡፡ ሐሳብ ለሐሳብ ከሚለዋወጡት ውስጥ የተማሩት ከልተማሩት፤ ያልተማሩት ካልተማሩት፤ የተማሩት ከተማሩት ይጨቃጨቃሉ፡፡ ኢኮኖሚው አድጓል አላደገም፤ ለምቷል አለማም፤ አድጓል ግን አለማም፤ ለምቷል ግን አላደገም፤ የንትርኩ ጭብጦች ሆነዋል፡፡ ሁሉም የራሱን ሐሳብ እንጂ የሌላውን ሊቀበል አይፈልግም፡፡ የማንኛቸውም ማስረጃ ውኃ አይቋጥርም፤ ለሌላውም አይዋጥም፡፡ ውይይቱና ክርክሩ በእውነት ስለ እውነት ሳይሆን ኢሕአዴግንና ኢሕአዴግ መራሹን መንግሥት ከመውደድና ከመጥላት የተነሳ ነው፡፡
በጽንሰ-ሐሳብ ላይ ያልተመሠረተ አመለካከት የግል ወይም የቡድን ብቻ ነው፡፡ ሙግቱም በተጨባጭ ሁኔታ ላይ ያልተመሠረተ ፍሬ ከርሲኪ ሊሆን ስለሚችል፣ ስህተትን ለማስረዳት የሚችል ብቃት አይኖረውም፡፡ ለዚህም ነው፣ ኢኮኖሚው አድጓል የሚሉም፣ አላደገም የሚሉም፣ ለማደጉም ላለማደጉም፣ ለመልማቱም፣ ላለመልማቱም፣ ለመሻሉም፣ ላለመሻሉም ማረጋገጫ የሌላቸው፡፡ ሙግታቸውም ከመውደድና ከጥላቻ፣ ከማመንና ከመጠራጠር የመነጨ ብቻ የሚመስለው፡፡ ለማደጉም ላለማደጉም፣ ለመልማቱም ላለመልማቱም፣ አድጎ ላለመልማቱም፣ ለምቶ ላለማደጉም የሚቀርቡት ማስረጃዎች ምንጫቸው ሁለት ነው፡፡ አንዱ ለመንግሥት የኢኮኖሚ ባለሟሎች በቀር ለሌሎች ሰዎች የማይታይ ቢታይም የማይቀበሉት በባለሟሎቹ የሚዘጋጅ ስታቲስቲካዊ መረጃ ሲሆን፣ ሌላው ለመንግሥት ባለሟሎችና ባለሥልጣናት የማይታይ ቢታይም የማይቀበሉት ለአብዛኛው ሕዝብ በገበያ ውስጥ የሚታይ የኑሮ ሁኔታ ነው፡፡
በፖለቲካ እምነት ልዩነት ላይ ጥራዝ ነጠቅ ዕውቀት ተደርቦ መጠላላቱና መናናቁ ስለ