ለለይቶ ማቆያና ማከሚያ ማዕከልነት ሲያገለግሉ የነበሩ ዩኒቨርሲቲዎች የጥንቃቄ ፕሮቶኮልን በማሟላት ተማሪ መቀበል እንደሚችሉ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትሩ ዶክተር ሳሙኤል ኡርቃቶ ገለጹ።
–
በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አዘጋጅነት ትናንት በሀዋሳ ከተማ የተጀመረው የውይይት መድረክ እንደቀጠለ ነው።
–
ሚኒስትሩ ከመድረኩ በተጓዳኝ ለጋዜጠኞች እንደገለጹት አንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን ለመከላከል በመንግስት ሲከናወን የነበረውን ተግባር ለማገዝ ለለይቶ ማቆያና ማከሚያ አገልግሎት ሲሰጡ ነበር።
–
በነዚህ ተቋማት የኬሚካል ርጭት በማድረግ በተገቢው መንገድ የማጽዳት ስራ መከናወኑን አመልክተው የጤና ሚኒስቴር ባለሙያዎችም በተገቢው የሚፈትሹበት ሁኔታ እንደሚኖር ተናግረዋል።
–
ተማሪዎች ከቤታቸው ተነስተው ዩኒቨርሲቲ እስከሚደርሱበት ጊዜ ድረስ ተጋላጭነት እንዳይኖር እያንዳንዱ ተቋም በተገቢው በመፈተሽ ጥንቃቄ የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል።
–
በጤና ሚኒስቴር በተቀመጠው የጥንቃቄ ፕሮቶኮል መሰረት ተቋማት መስፈርቱን አሟልተው ዝግጁ ሲሆኑ ተማሪ መቀበል እንደሚችሉ አስታውቀዋል።
–
የተማሪ መቀበያ ጊዜም በዩኒቨርሲቲዎቹ በሚዘጋጅ መርሀ ግብር መሰረት እንደሚከናወንና ለመጀመሪያው ዙር የሚቀበሉት ተመራቂዎችን እንደሆነ አስረድተዋል።
–
በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አዘጋጅነት በሀዋሳ ከተማ እየተካሄደ ባለው የውይይት መድረክ ሚኒስትሮችና የሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ፕሬዝዳንቶች እየተሳተፉ ናቸው ሲል ኢዜአ ዘግቧል።