ለለይቶ ማቆያና ለኮሮና ቫይረስ ማከሚያ ማዕከልነት ሲያገለግሉ የነበሩ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎችን መቀበል ሊጀምሩ ነው

ለለይቶ ማቆያና ማከሚያ ማዕከልነት ሲያገለግሉ የነበሩ ዩኒቨርሲቲዎች የጥንቃቄ ፕሮቶኮልን በማሟላት ተማሪ መቀበል እንደሚችሉ የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትሩ ዶክተር ሳሙኤል ኡርቃቶ ገለጹ።
በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አዘጋጅነት ትናንት በሀዋሳ ከተማ የተጀመረው የውይይት መድረክ እንደቀጠለ ነው።
ሚኒስትሩ ከመድረኩ በተጓዳኝ ለጋዜጠኞች እንደገለጹት አንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች የኮሮና ቫይረስ ስርጭትን ለመከላከል በመንግስት ሲከናወን የነበረውን ተግባር ለማገዝ ለለይቶ ማቆያና ማከሚያ አገልግሎት ሲሰጡ ነበር።
በነዚህ ተቋማት የኬሚካል ርጭት በማድረግ በተገቢው መንገድ የማጽዳት ስራ መከናወኑን አመልክተው የጤና ሚኒስቴር ባለሙያዎችም በተገቢው የሚፈትሹበት ሁኔታ እንደሚኖር ተናግረዋል።
ተማሪዎች ከቤታቸው ተነስተው ዩኒቨርሲቲ እስከሚደርሱበት ጊዜ ድረስ ተጋላጭነት እንዳይኖር እያንዳንዱ ተቋም በተገቢው በመፈተሽ ጥንቃቄ የሚያደርግ መሆኑን ገልጸዋል።
በጤና ሚኒስቴር በተቀመጠው የጥንቃቄ ፕሮቶኮል መሰረት ተቋማት መስፈርቱን አሟልተው ዝግጁ ሲሆኑ ተማሪ መቀበል እንደሚችሉ አስታውቀዋል።
የተማሪ መቀበያ ጊዜም በዩኒቨርሲቲዎቹ በሚዘጋጅ መርሀ ግብር መሰረት እንደሚከናወንና ለመጀመሪያው ዙር የሚቀበሉት ተመራቂዎችን እንደሆነ አስረድተዋል።
በሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር አዘጋጅነት በሀዋሳ ከተማ እየተካሄደ ባለው የውይይት መድረክ ሚኒስትሮችና የሁሉም ዩኒቨርሲቲዎች ፕሬዝዳንቶች እየተሳተፉ ናቸው ሲል ኢዜአ ዘግቧል።