የዶ/ር አብይ ችግር ባረጃ ጎማ/መኪና ህዝብን ለማሻገር መሞከራቸው ነው #ግርማካሳ

ለዶ/ር አብይ፣ ለአቶ ለማ መገርሳና ለአቶ ገዱ አንዳርጋቸው ትልቅ አክብሮት አለኝ። የለማ ቲም ለሚባለው ማለት ነው። አቶ ገዱና አቶ ለማ ከክልል ርእስ መስተዳደርነት ለቀዋል። ዶ/ር አብይ ግን አሁንም በሃላፊነታቸው ላይ ነው ያሉት።የፈለገውን የማድረግ አቅም ግን የላቸውም።

ሕጋዊ ስልጣን  አላቸው። ጠቅላይ ሚኒስተር እንደመሆናቸው በሕግ መንግስቱ መሰረት ተጠሪነታቸው ለፓርላማው ነው። ግን በኢሕአዴግ ኢትዮጵያ ከሕግ መንግስቱ በተጻራሪ ፓርላማው ሳይሆን ፓርቲው ነው ትልቅ ስልጣን ያለው። ከአንድ የፓርላማ ተወካይ ይልቅ፣ አንድ የኢሕአዴግ አባል የበለጠ የፖለቲካ ሃይል አለው። በፓርቲው አሰራር ደግሞ ፣ የፓርቲው አመራሮች ነው በጋራ የሚወስኑት።

አሁን ባለው የኢሕአዴግ አሰራር ፣ድርጅቱ የወሰነዉን ነው ጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚያስፈጽሙት። አብዮታዊ ዲሞክራሲ የሚለው ፣ ድርጅታዊ ማ’እከላዊነት የጠበቀ አሰራር ማለት ነው። ከድርጅቱ ውሳኔ ውጭ ምንም ማድረግ አይችሉም።

በፓርላማ የሕወሃትና የኦህዶእድ/ኦዴፓ ተወካዮች ድምጻቸው ከ 210 አይበልጥም። የደሃዴንና የአዴፓ/ብአዴን ተወካዮች ከ280 በላይ ናቸው። 547 ወንበሮች ባለው ፓርላማ አብልጫ ድምጽ ነው ያላቸው።በኢሕአዴግ ድርጅቱ ውስጥ ከሄድን ግን ህወሃትና ኦህዴድ በጋራ ሆነው ግማሹን መቀመጫ ይዘዋል። ህወሃት ብቻ በፓርላማ 6.5% መቀመጫ ሲኖራት በኢሕአዴግ ውስጥ ግን 25% መቀመጫ ነው ያላት። በዚህ ምክንያት አብዛኛው ኦህዴድ/ኦዴፓዎች ህወሃቶች የተጀመረዉን ለውጥ ስለማይፈልጉ፣ ዶ/ር አብይ በድርጅቱ ውስጥ ያንን ያህል ስልጣን የለውም። ድርጅቱን አሳምኖ ድርጅቶ ካልወሰነ በቀር እንደ ጠቅላይ ሚኒስትር እጁ የታሰረ ነው።

ይሄንን ካለመረዳት ይመስለኛል ብዙ ወገኖች በዶ/ር አብይ ላይ ያላቸው ተስፋቸው መሟጠጥ አይደለም ወደ ተቃዋሚነት መሸጋገር የጀመሩት።

ይሄን አብዮታዊ ዲሞክራሲያዊ አስራር ለማፍረስና መሰረታዊ የፕሮግራም መሻሻሎች ለማምጣት አብዛኞችን  ኦህዴዶችንና ሕወሃቶች ማቀፍ ያስፈልጋል። ያንን ማድረግ አልተቻለም። ደሃዴኖች ደካማ አመራሮች ነው ያሏቸው። አዴፓ/ብአዴኖች ደግሞ፣ እነ ዶር አምባቸው  ጡንቻቸውን ማሳየት አልቻሉም። እንወክለዋለን የሚሉትን ማህበረሰብ የሚመጥን ስራ እየሰሩ አይደለም። እንደውም ይሄን ማህበረሰብ ባወረደ መልኩ ነው ኢሕአዴግ ውስጥ እንደ ልፍስፍ እየተንቀሳቀሱ ያሉት።

ስለዚህ በአጭሩ፣ ለውጡን ወደፊት ማስገስገስ አልተቻለም። በኢሕአዴግ ውስጥ ያለው ግሪድሎክ ነው። ሾፌሩን ቢቀየርም መኪናው አልተቀየረም። ስለዚህ የፈለገ ጥሩ ሹፌር ቢኖር መኪናዋ አሮጌ፣ ጎማዎቹ  የተበላሸሹ  እስከሆኑ  ድረ መጓዝ አይቻልም።አዲስ መኪና፣ አዲስ ጎማ መኖር አለበት። የአብዮታዊ ዲሞክራሲ አሰራር መቅረት አለበት።

ለዚህም እንዲረዳ  አንዱን ትልቁ ተስፋ የነበረው የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶች ማዋህድ ነበር። ዶ/ር አብይ አህመድ ያ እንደሚሆን በአዋሳው ጉባዬ ከዚያም በኋላ በርካታ ጊዜ የተናገሩ ሲሆን በዚያ ረገድ ግን እትስፋ የሚሰጥ ነገር አይታይም። ዉህደቱን በብቸኝነት ማለት ይችላል ኦህዴድ/ኦዴፓ የእግር ብሬክ እንዳደረገበት ነው እየተሰማ ያለው።

ከዚህም የተነሳ ዶ/ር አብይ መሰረታዊ ስራዎች ተግባራዊ ማድረግ ስላልቻሉ፣ በተቻለ መጠን ማድረግ የሚችላቸውን ስራዎች ፣ ችግኝ ተከላ፣ ሱዳን ሄዶ ማስታረቀ… የመሳሰሉትን ብቻ መስራት ሆኗል ስራቸው።

አሁንም የምመክረው፣ ዶ/ር አብይ ጽንፈኛ ኦህዴዶች/ኦዴፓዎች ማባባል አቁሞው፣ ዉህደቱን በቶሎ አጠናቀው ፣ ላለፉት ሃያ ስምንት አመታት የነበረው የዘር ፖለቲካ ግሳንግስ አራግፈው ፣ ትልቅ አማራጭ ይዘ እንዲወጡ  ነው። ለህዝብ ቃል የገቡትን፣ የሰበኳትን ታላቂቷን ኢትዮጵያ በወሬና አሮጌ ጎማ ያላት መኪና በማሽከርከር ማምጣት አይቻልም። ሕዝብ የእርሷን ንግግር ቋቋ እስኪለው ድረስ ጠግቧል። ህዝብ የሚፈለገው ተግባር ነው። ያንን ተግባር መፈጸም ካልቻሉ ደግሞ እውነቱን ለኢትዮጵያ ህዝብ ተናግረው ፣ ህዝብ መፍትሄ እንዲፈልግበት ያድርጉ።