ለሚመለከተው ሁሉ
ጉዳዩ፡- ከኢዜማ መለየታችንን ስለማሳወቅ!
ላለፉት 30 ዓመታት የኢትዮጵያ ሕዝብ የሥልጣን እና የሀገሩ ባለቤት እንዲሆን የአንድነት ኃይሉ አካላት የሆንን ሁሉ ከሕዝባችን ጋር ሆነን በሀገራችን ፖለቲካ ውስጥ ከፍተኛ መስዋዕትነት የከፈልን እና እየከፈልን የቆየን መሆናችን አይካድም።
እኛም (ፓርቲውን በስራ አስፈጻሚ ደረጃ ስንመራ የነበርን) እንደ ሌላው አባል ሁሉ ባለፉት የትግል ዓመታት በተደረገው ትግል ውስጥ ተሳታፊ የነበርን የዚህ ትውልድ አካል የሆነው በሕዝብ መስዋዕትነት በተገኘው እና በተስፋ በቀረው የለውጥ ጅማሮ አንድ ትልቅ ሀገራዊ ፓርቲ እንደሚያስፈልግ አምነን ያለንን ሁሉ አዋጥተን “ኢዜማ” የሚባል ሁሉን አሰባስቦ የሚያቅፍ፣ ለአንድነት ኃይሉ መሰባሰቢያ ይሆናል ብለን በማለም ሀገር አቀፍ ፓርቲ እንዲሆን መመሥረታችን የሚታወስ ነው።
በጋራ በመሠረትነው ኢዜማ ፓርቲ ውስጥ በአንዳንዶቻችን መሀል መጠነኛ የአቋም ልዩነት ቢኖረንም በሂደት በውይይት እንዲሁም መሬት በረገጠ ሥራ ወቅት ልዩነቱ እየጠበበ እና እየተስተካከለ ይሄዳል በሚል ቅን እሳቤ፤ በወንድማማችነት መንፈስ አምነን ነበር የተቀበልነው፡፡ ሆኖም ብዙም ሳይቆይ የአቋም ልዩነቱ ላይ የአካሄድም ልዩነት ተጨምሮበት ትግላችን መስመር ስቶ ከፍተኛ በሆነ በውስጠ ፓርቲ ትግል ውስጥ ተጠልፈን እንድንቆይ አድርጎናል፡፡
የኢትዮጵያ አሁን ሕዝብ በታሪኩ ገጥሞት የማያውቅ እዚህ መከራ ውስጥ ከመግባቱ በፊት መንገዳችንን እንድናስተካክል በፓርቲው ውስጥም በብዙ ታግለናል፡፡ በፓርቲው ጉባኤዎች ሁሉ ሳይቀር ስህተቶች ይታረሙ ይሆናል በማለት የትግሉን መድረክ ለማስፋት ብንሞክርም በተለያዩ ውስጣዊ እና ውጫዊ ምክንያቶች ማሳካት አልተቻለም፡፡ ኢዜማን ጠግኖ ለማዳን ያደረግነው ትግልም ከንቱ ቀርቷል፡፡
አሁንም በግልፅ እየታየ እንደሚገኘው የኢዜማ ከፍተኛ አመራር ሀገርን ለመታደግ ሕዝብንና ፓርቲዎችን አስተባብሮ ከማታገል ይልቅ አገዛዙ እየፈፀመ ላለው ሀገር አቀፍ ግፍ ድጋፍ እየሰጠ ይገኛል፡፡ ለዚህ ሥርዓት ምሶሶ እና ማገር ሆኖ በማገልገል የአንድነት ኃይሉን አቅም አላባ በማድረግ ከፍተኛ ሚና እየተጫወተ ለመሆኑ የአባላት ብቻ ሳይሆን የሕዝብም ቅሬታ ሆኖ በመሰማት ላይ ይገኛል፡፡
ይህም ኢዜማ ከቆመላቸው መሠረታዊ አላማዎች፤ መርሆች እና እሴቶች በመውጣት የገዢውን ቡድን እሴቶች እና አላማዎች እያራመደ እንደሆነ ግልፅ ሆኗል፡፡በዚህም ኢዜማ የተለየ ቁመና የሌለውና ተክለ ሰውነቱም ሆነ ህልውናው በየዕለቱ ለትውልድ የሚተላለፍ ጠባሳዎችን ጥሎ ከሚያልፈው አገዛዝ የተለየ እንዳይመስል ተደርጎ እየተሠራ እንደነበር አሁን ለበርካታ ወገኖች ግልፅ ሁኗል፡፡
በተለያዩ ወቅቶች እና ሁኔታዎች በአባላት ለፓርቲው አመራር የሚቀርቡ ጥያቄዎችን ተቀብሎ ለጤናማ ውይይት እና ለንግግር ዝግጁ ከመሆን ይልቅ ንቁ አባላቶችን በተለያዩ ፍረጃ ከደንብ እና አሰራር ውጪ ለማሸማቀቅ ሲሞከር በተደጋጋሚ ተመልክተናል፡፡ በፓርቲው አደረጃጀት ነፃ እና አሳታፊ የሆነ ውይይት ለማድረግ እንዳይከፈት ሆኖ አሁን ባለው አመራር በሩ ተዘግቷል፡፡
በዚህና በሌሎች በርካታ ምክንያቶች ፓርቲውን ማዳን በማይቻልበት ሁኔታ ላይ ተደርሷል። ሰሚ በመታጣቱ እንጂ የራሱን ህብረ ቀለም በማጣቱ ራሱን እንዳከሰመ ፓርቲ ከቆጠርነው ቆይተናል። ይህንን ከፓርቲው መድረኮች ባሻገር በአደባባይ ተናግረናል፡፡ በኢዜማ ለውጥ ለሚፈልጉ ለሕዝብ እና ለእውነት ለወገኑ ፖለቲከኞች አዲስ ነገር ባይሆንም የፓርቲውን 4ኛ ምሥረታ ዓመት አስመልክተው የፓርቲው መሪ ባደረጉት ንግግር ያረጋገጡት የሚመሰክረው እውነትም ይሄንኑ ነው፡፡
ከላይ እንደተጠቀሰው ምንም እንኳን ያለመታከት የውስጥ ትግል ያደረግን ብንሆንም በሂደቱ ለደረሰው ፖለቲካዊ ኪሳራ እኛም ከተወቃሽነት ልናመልጥ እንደማንችል እናውቃለን፡፡ ከአራት ዓመታት በላይ በውስጥ ትግል ተወስነን የተጓዝነው “ተባብራችሁ ሥሩ” የሚለውን የኅብረሰተሰብ ክፍል እና ደጋፊን ላለማሳዘን፣ በውስጥ እየታገልን ቆይተን መፍትሔ ለማምጣት ነበር፡፡ ከዚህ በላይ አብሮ መቆየት ግን ተጨማሪ ብዥታን እና የሌለ ተስፋን እንዲጠበቅ የሚያደርግ በመሆኑ ለሕዝብ፤ ለአባላት እና ለደጋፊዎች ግልፅ መሆን ይኖርበታል፡፡ በታሪክ እና በሞራል ተጠያቂ ላለመሆን በእነዚህ እና አስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ በሂደት በምንገልጻቸው በርካታ ምክንያቶች ፓርቲውን ወደ ሃዲዱ ለመመለስ ያደረግነው ትግል ግቡን ስላልመታ ራሳችንን ከኢዜማ አባልነት ያገለልን መሆኑን እንገልጻለን፡፡
የኢዜማን አመራር አምኖበት ከሚፈጽመው ተግባር ለመመለስ እና ፓርቲውን ለማዳን በትዕግስት ለታገላችሁ የፓርቲው አባላት እና ደጋፊዎች እንዲሁም ከመጀመሪያው ጀምሮ ፓርቲው አቋሙን እንዲያርም ገንቢ ትችት ስትለግሱ ለነበራችሁ ሁሉ ያለንን አድናቆት እና ክብር በዚሁ አጋጣሚ ልንገልፅ እንወዳለን፡፡
ሰላም ፤ አንድነት እና ፍትህ ለሕዝባችን!
አቶ የሽዋስ አሰፋ 5. ወ/ሮ ናንሲ ውድነህ
አቶ ሀብታሙ ኪታባ 6. አቶ የጁአልጋው ጀመረ
አቶ ተክሌ በቀለ 7. አቶ ኑሪ ሙደሲር
አቶ ዳንኤል ሺበሺ