ግድያውም የመንግስት የማይፈጸሙ ቃላቶችም ቀጥለዋል !

ግድያውም የመንግስት የማይፈጸሙ ቃላቶችም ቀጥለዋል !

በታጠቁ ኃይሎች በተለያዩ ክልሎች በይብልጡኑ በኦሮሚያና ቤንሻንጉል ክልሎች በንጹሃን፣ ባልታጠቁ፣ ራሳቸውን መከላከል በማይችሉ ሕጻናት፣ ሴቶችና አዛውንቶች ላይ የሚደረገው ግድያ ቀጥሏል። ይህ ዘርን (በተለይ አማራን) መሰረት አድርጎ የሚፈጸመው ግድያ መንግስት የተለያዩ ቃሎችን ቢገባም ሊያስቆምም ወንጀለኞችንም ሊይዝ አሊያም መዋቅሩን ሊያጸዳ አልቻለም። ቃሉንም አልፈጸመም። ኮማንድ ፖስት በየስርቻው ማቋቋም የዜጎችን ግድያ ከማባባስ ውጪ ምንም አልፈየደም፤ ኮማንድ ፖስቱንም ይመራሉ የተባሉ ግለሰቦች ወታደራዊና የደሕንነት ልምዶቻቸው የሞተ መሆኑ አሊያም የፖለቲካ ተላላኪዎች ይመስል የሚዲያ ፍጆታ ከመሆን ባለፈ አንድም የረባ ስራ አልሰሩም።

ታጣቂዎችን ትጥቅ አስፈትተናል፣ ታጣቂዎችን ገድለናል፣ ከጥቃቱ ጀርባ ያሉትን የመንግስት አካላት ለፍርድ ልናቀርብ ነው፣ በጥቃቱ የተፈናቀሉ ወደ ቀያቸው መልሰናል፣ በ15 ቀናት ውስጥ ጥቃት አድራሾችን ደምስሰን ሰላም እናሰፍናለን ወዘተ … … ከሚሉ ቃልኪዳኖች ጀምሮ እስከ ጉዳዩ በክልሎች መሪዎች ውይይት ተደረገበት፣ ሰላምና ደሕንነትን ለመቆታተር የክልል መሪዎች ተነጋገሩ፣ ውይይት፣ስብሰባ፣ አጀንዳ ንግ ግር ወዘተ. ….. ተብሎ ተብሎ ወደፊትም ሲባል እንሰማለን ፤ ሆኖም ጥቃቱን ከማስቆም ይልቅ እየባሰበት ከመሔድም አልፎ በመዋቅር የተደገፈ በክልል ልዩ ኃይሎች መንገድ እስከመዝጋት ተደርሷል።

ጥቃቱን ማስቆም ያልተቻለው መንግስትም በቃሉ ሊገኝ ያልቻለው የጥቃቱ ምንጭ፣ የጥቃቱ መሰረት ፣ የጥቃቱ አራማጅ የመንግስት መዋቅር በመሆኑ ነው። በንፁሐን ላይ የሚደርሱ ጥቃቶች መንግስት ማስቆም ያልቻለው መዋቅሮችን የማጽዳት ፍላጎት ባለመኖሩ ነው። የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ዜጎች በተደጋጋሚ የሚናገሩት ነገር ቢኖር ጥቃቱ በመንግስት አመራሮች የሚደገፍ መሆኑን ነው በተጨማሪም ጥቃቱ ከመድረሱ በፊት በየአከባቢው የሰፈረው የመንግስት ጦርና ልዩ ኃይል እንዲነሳ መደረጉና አከባቢውን ከመንግስት የጸጥታ ኃይሎች የማፅዳት ተግባሩ የመንግስትን አመራሮችና የመከላከያ ሹሞች ላይ እጅ እንዲጠቆም ሆኗል።

ባለፉት ሁለት ቀን ብቻ የተፈጸሙት ግድያዎች የመንግስትን ንዝሕላልነት ፍንትው አድርገው ያሳያሉ። መንግስት በትግራይ ሕግን አስከብራለሁ ብሎ ጦሩን እንዳዘመተ ሁሉ በሌሎችም ክልሎች ጦሩን አዝምቶ ንፁሃንን ከግድያ ሊታደጋቸው ይገባል። ኮማንድ ፖስት በየስርቻው ማቋቋም የዜጎችን ግድያ ከማባባስ ውጪ ምንም አልፈየደም፤ ኮማንድ ፖስቱንም ይመራሉ የተባሉ ግለሰቦች ወታደራዊና የደሕንነት ልምዶቻቸው የሞተ መሆኑ አሊያም የፖለቲካ ተላላኪዎች ይመስል የሚዲያ ፍጆታ ከመሆን ባለፈ አንድም የረባ ስራ አልሰሩም። የችግሩ መፍትሔ ያለው በመንግስት እጅና እጅ ብቻ ነው። #MinilikSalsawi