በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች ጸብ ሕይወት አጠፋ

በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች ጸብ ሕይወት አጠፋ

በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በተማሪዎች መካከል በተነሳ ጸብ የአንድ ተማሪ ሕይወት ማለፉን ዩኒቨርሲቲው አስታወቀ። ትናንት ምሽት በዩኒቨርሲቲው ዋና ግቢ በተከሰተው ጸብ የአንደኛ ዓመት የተፈጥሮ ሳይንስ ተማሪ ሕይወት ማለፉን የዩኒቨርሲቲው ፕሬዝዳንት ጽሕፈት ቤት ኃላፊ አቶ አየለ አዳቶ ለጀርመን ድምፅ ሬድዮ ገልጸዋል።

የተማሪው አስክሬን በአዲስ አበባ ምንሊክ ሆስፒታል ምርመራ ከተደረገለት በኋላ ወደ ትውልድ ስፍራው ወልዲያ መላኩንም የጽሕፈት ቤቱ ኃላፊ ተናግረዋል።

የነገሩ መነሻ የሁለት ተማሪዎች ጸብ መሆኑን የጠቀሱት አቶ አየለ ከጀርባው ሌላ ተልኮ ይኑረው ወይንም አይኑረው እየተጣራ ይገኛል ብለዋል። አክለውም «በአሁኑ ወቅት ከግድያው ጋር በተያያዘም 44 ተማሪዎች በቁጥጥር ሰር ውለው በፖሊስ ምርመራ እየተደረገባቸው ይገኛል።» ብለዋል።

«የዩኒቨርሲቲው ማኅበረሰብም በተፈጠረው ሁኔታ በከፍተኛ ሀዘን ውስጥ ቢገኝም የመማር ማስተማሩ ሂደት ግን ሳይቋረጥ ቀጥሏል» ሲሉም አክለዋል። የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ እስካሁን ሰላማዊ ድባብ ከሚስተዋልባቸው ጥቂት የአገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎች መካከል አንዱ በመሆን ይታወቃል።

አሁን የተባለው ጸብ የተነሳውና የሰው ሕይወትም ያለፈው ተማሪዎቹ ከፊታችን ሰኞ ጀምሮ የአንደኛ ወሰነ ትምህርት ፈተና ለመውሰድ በዝግጅት ላይ ባሉበት ውቅ ነው።

(የጀርመን ድምፅ ሬድዮ)