ተሞከረ ከተባለው መፈንቅለ መንግስት ጋር በተያያዘ የአብን አባላት እየታሰሩ ነው።

የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ ( አብን ) ተሞከረ ከተባለው መፈንቅለ መንግስት ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባ እና ኦሮሚያ ክልል ከ 100 በላይ የፖርቲው አባላትና አባል ያልሆኑ ሰዎች መታሰራቸውን ይፋ አደረገ።የፖርቲው የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ክርስቲያን ታደለ እንዳሉት ግለሰቦቹ እየተያዙ ያሉት መፈንቅለ መንግስቱን በማቀናበር አብን አለበት በሚልና ፣ የገንዘብ ድጋፍ ታደርጋላችሁ በሚል መታሰራቸውን ፤ አንዳንዶቹም የት እንደታሰሩ እንደማይታወቅ ተናግረዋል።ጉዳዩ ህዝብን ወደ አለመረጋጋት፣ ሀገሪቱንም ወደባሰ ሁኔታ የሚያስገባ በመሆኑ ድርጊቱ በአስቸኳይ እንዲቆም ፣ የተያዙትም እንዲለቀቁ ጠይቋል። ይህ የማይሆን ከሆነ ግን ጉዳዩን ለህዝብ በማሳወቅ ህዝቡ በመንግሥት ላይ ጫና እንዲያሳድር እናደርጋለን ሲሉ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊው ለ DW ተናግረዋል። መንግሥት ከዚሁ የመፈንቅለ መንግሥት ተግባር ካለው ጉዳይ ጋር በተያያዘ ትናንት ስድስት ሰዎችን በሽብር ከስሶ ፍርድ ቤት ማቅረቡን መዘገባችን ይታወሳል።