አቶ ጌታቸው ረዳ አዲስ አበባ ላይ ከብሊንከን ጋር መገናኘታቸውንና መምከራቸውን ገልጸዋል።

የአሜሪካው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በአዲስ አበባ የስራ ጉብኝት ባደረጉበት ወቅት ከህወሓት አመራሮች አንዱ ከሆኑት አቶ ጌታቸው ረዳ ጋር ውይይት አድርገው ነበር።

አቶ ጌታቸው ረዳ አዲስ አበባ ላይ ከብሊንከን ጋር መገናኘታቸውንና ስለ ሰላም ስምምነቱ አተገባበር እድገት እና ስላሉት እንቅፋቶች ዙሪያ መምከራቸውን ገልጸዋል።

አቶ ጌታቸው ፤ በውይይቱ ወቅት ለሰላም ያላቸውን የማይናወጥ ቁርጠኝነት እንዲሁም ሰላምን ለማደፍረስ የሚንቀሳቀሱ ሃይሎች የሚፈጥሩትን ተግዳሮቶች ለመወጣት በእነሱ በኩል ያላቸው የማያወላዳ ቁርጠኝነት እንዳረጋገጡ ገልጸዋል።

” ጊዜያዊ አስተዳደር መመስረትን ጨምሮ በህዝባችን ላይ እየደረሰ ያለውን ስቃይ ለመቅረፍ በሚደረገው ጥረት ሁሉ እንቅፋት የሆኑ ችግሮችን ለመፍታት የበኩላችንን ለመወጣት ዝግጁ ነን ” ሲሉም ገልፀዋል።

ከዚህ በተጨማሪ አቶ ጌታቸው ረዳ ከብሊንከን ጋር በነበረው ውይይት በትግራይ ውስጥ እና በትግራይ ላይ በተደረገው ጦርነት ለተፈጸሙ ወንጀሎች ተጠያቂነትን ማረጋገጥ አስፈላጊት ላይ ሃሳባቸውን እንዳካፈሉ አመልክተዋል።

አቶ ጌታቸው፤ ጠንካራ የሽግግር የፍትህ ማእቀፍ ተቀባይነት ያለውና የሚያስመሰግን ቢሆንም በትግራይ ለተፈፀሙ ወንጀሎች ተጠያቂነት ከሀገራዊ ማዕቀፍ የዘለለ በመሆኑ ዓለም አቀፍ ጥረቶች አስፈላጊ ናቸው የሚል አቋማቸውን እንደገለፁ አስረድተዋል።

አንቶኒ ብሊንከን በበኩላቸው ፤ ሀገራቸው አሜሪካ የሰብአዊ ድጋፍን ለማጠናከር፣ ለመልሶ ማቋቋም ሃብት ለማሰባሰብ፣ እንዲሁም በኢትዮጵያ እና በመላው ቀጣናው ሰላምና መረጋጋት እንዲሰፍን ከስምምነቱ ተዋናይ ወገኖች ጋር በጋራ እንደምትሰራ በድጋሚ ቁርጠኛ መሆኗን አረጋግጠዋል ሲሉ አቶ ጌታቸው ረዳ በይፋዊ የማህበራዊ ትስስር ገፃቸው ላይ አስፍረዋል።