ለአፋር ህዝብ ያለን አጋርነት በተመለከተ ከአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ(አብን) የተሰጠ መግለጫ

በአጭር ጊዜ ውስጥ በተለይም በአማራ ክልል ተደራሽነቱን ያሰፋው በወጣት አመራሮች የሚመራው የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) በአፋር ክልል በአፋሮች ላይ እየተፈጸመ ያለው ኢሰባአዊና ሕገ ወጥ እርምጃ አዉግዟል። የአፍር ህዝብ ለኢትዮጵያ አንድነይ ያደረገውና የከፈለውን ትልቅ መእስዋትነት በመረጃ ያስቀመጠው የአብን መግለጫ አፋሮች ለፍትህ፣ ለመንብት፣ ለነጻነትና ለእኩልነት ከሚያደረጉት ትግል ጋር አግር ሆኖ እንደሚቆምም ገልጿል።

አብን በአዲስ አበባ ዙሪያ በተለይ በጋሞ ማህበረሰብ ላይ ራሳቸውን ቄሮ ብለው በሚጠሩ አክራሪዎች የተፈጸመዉን አሰቃቂ ተግባር ከማውገዝ አልፎ ተሰደው በአዶዲስ አበባ ለሸሹ ስደተኞችም በቀዳሚነት አጋር ሆኖ የቆመ ድርጅት ሲሆን፣ በአዲስ አበባም በአዲስ አበቤዎች ላይ የደረሰውን የጅምላ እስር በቀድሚነት ያወገዘ ድርጅት ነው። አሁንም በአፋር ወገኖች ላይ የደረሰውን ግፍ በመቃወም ፣ የአፍር የመብት ታጋዮች ድምጽ ሆኖ የወጣ ብቸኛ የተቃዋሚ ድርጅት አብን መሆኑን እናያለም።

ለአፋር ህዝብ ያለን አጋርነት በተመለከተ ከአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ(አብን) የተሰጠ መግለጫ
===================================
የአፋር ህዝብ በኢትዩጵያዊነቱና በነፃነቱ እንደማይደራደር እና ገድሉም በታሪክ ማህደር በደማቅ ቀለም የተፃፈ ህዝብ ነዉ። የአፋር ወገኖቻችን የኢትዩጵያዊነታቸዉን ጥልቅ ፍቅር ሲገልፁት “አረንጓደ ቢጫና ቀዩን የኢትዬጵያ ሰንደቅ አላማ እንኳን እኛ ግመሎቻችን ከርቀት ይለዩታል” በማለት ነዉ።

የአዉሳ ሱልጣኔት ተብሎ የሚታወቀዉ የአፋር ህዝብ ግዛት እጅግ ታሪካዊና ሰፊ ነበር። በኢትዬጵያ የነፃነት ትግል ታሪክ ዉስጥ የአፋር ህዝብ ተጋድሎ ጉልህ ነዉ። በ1885 እኤአ ሀገራችንን ለመዉረር የዘመተዉን የግብፅ ጦር ከነጦር መሪዉ ወርነር ሙዚንገር ጭምር የደመሰሰዉ ጀግናዉ የአፋር ህዝብ ነዉ። “Sultan Mahammad Ibn Hanfadhe defeated and killed Werner Munzinger in 1875, who was leading an invading Egyptian army into Ethiopia.” በሚል የታሪክ ጠበብት ጽፈዉታል።

የአፋር ህዝብ ከአማራ ህዝብ ጋር በጥልቅ የሀገር ፍቅር፣ ነፃነትን በተመለከተ ባለዉ አቋም፣ በታሪክ፣ በበጎ አብሮ መኖር እና በባህል ከፍተኛ ቁርኝት ያለዉ ነዉ። ነገር ግን የአፋርንና የአማራን ህዝብ ታሪክና ግንኙነት በማጠልሸት ሁለቱንም ህዝብ በማዳከም ህወሀት የራሱን
ጠባብ አጀንዳ ጭኖባቸዉ ከርሟል። ሆኖም የአማራ ህዝብ የህወሀትን አገዛዝ አከርካሪ ሰብሮ የግፍ አገዛዙን መገርሰስ ተከትሎ ያፈገፈገዉን ሀይል በተዘረፉት በአማራ (የራያና የወልቃይት) ግዛቶችና በአፋር ህዝብ ላይ በማሰማራት ግልፅ ዘመቻ እያካሄደ ይገኛል።

በህወሀት የአገዛዝ ዘመን የአማራ ህዝብ የደረሰበትን የግፍ ካታሎግና ዝርዝር ቆጥሮ መጨረስ አይቻልም። በተመሳሳይ መልኩ የአፋር ህዝብ በስሙ ሲነገድበት የቆየ መሆኑ ይታወቃል። ህወሀት የትግራይ ደም አላቸዉ የምትላቸዉን እንደራሴዎች በመመልመል እና በአፋር ህዝብ ላይ በመሾም አጠቃላይ የህዝቡን መብቶችና ነፃነቶች ስትጋፋ መቆየቷ ይታወቃል።

ወያኔ ዘላቂ ጥቅሟን ለማስከበርና የኮንትሮባንድ ሸቀጦችን በስዉር ለማስተላለፍ ያስችላት ዘንድ በድንበርና በመተላለፊያዎች አካባቢ ያሉትን የአማራና የአፋር ህዝብ እርስበርስ እንዲጋጩ ለማድረግ ስትታትር መቆየቷም ይታወቃል። በተለይ የሁለቱ ህዝቦች በታሪክና በባህል ያዳበሯቸዉን የጋራ አሰራሮች በመጠቀም ግንኙነት እንዳይፈጥሩ የወያኔ አገዛዝ በመካከላቸዉ አጥር ሆኖ ቆይቷል።

በቅርቡ ጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አህመድ በአፋር ባደረጉት ጉብኝት ወቅት ችግሩን የተረዱና ይፋ ሊያደርጉ የሚችሉ ሰዎችን እንዳይገኙ በማድረግ ፕሮፖጋንዳ ስታሰራጭ መቆየቷ ይታወሳል። Truth cast to Earth shall rise again (እዉነት
ትመነምናለች እንጂ አትበጠስም) እንዲሉ የአፋር ህዝብ እዉነተኛ ፍላጎትና ትግል እዉን ሆኖ ባደባባይ ዉሏል።

የአፋር ህዝብ የወያኔን አገዛዝና መሰሪ ተግባር በማዉገዝ የተቃዉሞ እንቅስቃሴ በይፋ ጀምሯል። የአፋር ህዝብ በልጆቹ እንጂ በህወሀት ቅጥረኞች ሊተዳደር አይገባም በሚል መሪ መፈክር ዛሬ ተቃዉሞዉን አስተጋብቷል። ነገር ግን ዛሬም እንደተለመደዉ ሰላማዊዉን የአፋር ህዝብ በጠመንጃ ለማንበርከክ ተሞክሯል።

በሰላማዊዉ የአፋር ወገናችን ላይ በተተኮሰ የጥይት ሩምታ ምክንያት የተቃዉሞ ሰልፉ ለጊዜዉ በሀይል እንዲበተን ተደርጓል። በዚህም በርካታ የአፋር ወገኖቻችን ላይ መንገላታትና መቁሰል እንደደረሰ ለመረዳት ችለናል።

የአማራ ብሄራዊ ንቅናቄ (አብን) የተጎዱት እንዲያገግሙ እየተመኘን ወንድም የሆነዉ የአፋር ህዝብ በሚያደርገዉ እልህ አስጨራሽ የመብት እና የነፃነት ትግል ጎን የምንሰለፍ መሆኑን ለማረጋገጥ እንወዳለን።

አብን