አዲስ አበቤዎች ብልፅግናን ብቻ ነዉ የመረጡት? የትግራይ ክልል እጣ ፈንታስ ምን ይሆናል?

DW : የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ሰኔ 14፤ የተካሄደዉን 6ኛዉን ብሔራዊ ምርጫ ዉጤት ሐምሌ 8 ቀን፤ 2013 ዓም ይፋ አድርጓል። ዉድድር ከተደረገባቸዉ 436 የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫዎች መካከል ገዥዉ የብልፅግና ፓርቲ 410 ሩን አሸንፎአል። የተቃዋሚ ፓርቲዎች 11 የፓርላማ መቀመጫዎችን፤  የግል ተወዳዳሪዎች 4 የፓርላማ መቀመጫዎችን አሸንፈዋል። ድጋሚ ምርጫ የሚከናወንባቸው የፓርላማ መቀመጫዎች ብዛት ደግሞ 10 መሆኑ ተነግሮአል። በዚህ ምርጫ ቀሪ የህዝብ ተወካዮች ም/ቤት መቀመጫዎችን የሚይዘዉን ፓርቲ መለየት ቢቻልም በአጠቃላዩ ምርጫዉ ግን ገዥዉ ብልፅግና ፓርቲ ከተገመተዉ በላይ 97.44 % በማግኘት ማሸነፉ ተረጋግጦአል። ይህ ዉጤት ብልፅግና ፓርቲ በሚመሰረተዉ መንግስት ዉስጥ ሕግን እስከማሻሻል የሚደርስ ስልጣን ይሰጠዋል ማለት ነዉ። በምርጫዉ የተሻለ ዉጤት ያስመዘግባሉ ተብለዉ የተጠበቁ አብዛኛዎቹ ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ከፍተኛ ሽንፈት ገጥሟቸዋል። እስካሁን ግን የምርጫዉን ዉጤት ሂደት አልቀበልም ያለ የፖለቲካ ፓርቲ አልታየም። አንዳንዶቹ ግን በምርጫዉ እዚህም እዝያም ስህተቶች እንደነበሩ በተለያዩ አጋጣሚዎች ይናገራሉ። 6ኛዉ ብሔራዊ ምርጫ፤ የተቃዋሚዎች ተስፋ፤ የሚመሰረተዉ መንግሥት እንዴትነት፤ በዚህ በዉይይታችን የምንዳስሳቸው ጉዳዮች ናቸው።

በዉይይቱ የተሳተፉት  

አቶ ኃይሉ አዱኛ ፤ የኦሮሚያ ክልል ብልጽግና ፓርቲ ጽ / ቤት የህዝብ ግንኙነት ምክትል ኃላፊ፤  አቶ ቸርነት ወርዶፋ የሕግ ጉዳይ ምሁር በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ መምህር፤ አቶ ያሬድ ኃይለማርያም የምስራቅ አፍሪቃና የአፍሪቃና ቀንድ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾች፤ ማህበር የኢትዮጵያ እና የአፍሪቃ ህብረት አስተባባሪ እንዲሁም፤  ተስፋሁን ዓለምነህ የአማራ ዴሞክራቲክ ኃይል ንቅናቄ ሊቀመንበርና የአማራ ክልል ፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ሰብሳቢ ናቸዉ። ተወያዮች በዚህ መድረክ ላይ ለመሳተፍ ስለቀረቡ በማመስገን ሙሉን ዉይይት የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን እንዲከታተሉ እንጋብዛለን።

መወያያ ነጥቦች

ምርጫዉ መጠናቀቁ እና ፓርቲዎችና ሕዝብ ውጤት በይሁንታ ተቀብሎ ወደ ብጥብጥ አለመግባቱ ይህ ከአሜሪካም የቅርብ ጊዜ ምርጫና ሂደቱ የተሻልንበት ሃቅ ነው የሚሉ እንዳለ ተሰምቶአል ምርጫዉን እንዴት አገኙት?  የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ለምክር ቤት ያልተመረጡ ተወዳዳሪ ፓርቲዎች ባይመረጡም አብረዉ መስራት እንደሚገቡ ቃል መግባታቸዉ በቀላሉ የማይታይ ጥሩ የፖለቲካ ባህል ልምምድ ጅምር ነው ያሉም አሉ። ይህን እርሶ እንዴት አገኙት? ምርጫው በተለይ አዲስ አበባ ላይ ተቃዋሚዎች አለመመረጣቸው ግራ ያጋባል ተብሎአል። እዉነት አዲስ አቤዎች ብልፅግናን ብቻ ነዉ የመረጡት ወይ ይላሉ? ባልደራስ ብዙ ደጋፊዎች እንደነበሩት የሚናገሩም አሉ። «አሁንም ፓርላማው በገዢ ፓርቲ ጠቅላይነት  መያዙ፤  ህዝብ አሁንም የሚፈልገውን እንዳላገኘ ግልፅ ማሳያ ነው፤ ከህወሓት ጊዜ ምንም ተሻለ አይደለም። ህወሓትም 99% አሽነፍያለሁ ሲል ፓርላማን ይይዝ ነበር»የሚሉ ትችቶችም እየቀረቡ ነው። የእርሶ አስተያየት እዚህ ላይ ምንድን ነዉ? «በኦሮሚያ ምርጫ ተደርጓል ማለት አይቻልም»የሚሉ አስተያየቶች ይሰጣሉ፤ ታዋቂዎቹ የኦሮሞ ፓርቲዎች አልተካፈሉም።በክልሉ ብልፅግና ቀርቦ ብልፅግና ብቻ ማሸነፉ ተነግሯል። የተሻለ ውድድር የታየውም አዲስ አበባ እና አማራ ክልል ላይ ብቻ ነው። ይህስ እንዴት ይገመገማል?  «ዋና ዋና የፖለቲካ ተቃዋሚ አባላት መታሰራቸዉን ተከትሎ ጠንካራ ፓርቲዎች ገለል ማለታቸው ትልቅ ጉድለት ነው» ተብሎአል። ይህ በምርጫዉ ላይ ተጽኖ አሳርፎአል ይላሉ? የቦርዱ ከላይ ከማዕከል የተሻለ ስራ መከወኑ ቢነገርለትም ልምድ የሌላቸው አዳዲስ የምርጫ ፈስፈፃሚዎች ብዙ ጉድለት የታየባቸውና ወደ ታች ወደ ወረዳ ሲወርድ ደግሞ መንግስት ከፍተኛ ተፅእኖ ያሳረፈበት ነበር፤ ነዉ ተብሎአል። ይህስ እንዴት ይገመገማል?  አጠቃላይ ይህ ምርጫ መልካም ልምድ የተቀሰመበት ቢሆንም በቀጣይ አምስት ዓመታት አገሪቱን አሁን ከገባችበት ዉጥንቅጥ እና ቀዉስ ሊያወጣ ይችላል ወይ ?  ከምርጫዉ በኋላ የትግራይ ክልል እጣ ፈንታ ምን ይሆናል?  በኢትዮጵያ አዲስ ከሚመሰረተዉ መንግሥት ምን እንጠብቅ?

ሙሉ ዉይይቱን የድምፅ ማድመጫ ማዕቀፉን በመጫን ይከታተሉ!