የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ኢትዮጵያና ሱዳን የገቡበትን ሰሞነኛ የድንበር ላይ ውዝግብ እንዲያረግቡ ጠየቀች፡፡

ኢትዮጵያ እና ሱዳን ሰሞነኛውን የድንበር ላይ ውጥረት እንዲያረግቡ ዩኤኢ ጠየቀች

የሱዳን ጦር በተደራጀ መንገድ ወደ ኢትዮጵያ ዘልቆ የመግባት እንቅስቃሴ እያሳየ መሆኑን የኢትዮጵያ መንግስት አስታውቋል

አል-ዐይን

ዩኤኢ ኢትዮጵያና ሱዳን የድንበር አለመግባባታቸውን በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ጠየቀች

ሀገራቱ ለቀጣናው ሰላምና መረጋጋት ትልቅ ሚና ስላላቸው የተፈጠረውን ችግር በንግግር እንዲፈቱ ዩኤኢ አሳስባለች

የተባበሩት አረብ ኤሚሬቶች ኢትዮጵያና ሱዳን የገቡበትን ሰሞነኛ የድንበር ላይ ውዝግብ እንዲያረግቡ ጠየቀች፡፡

የሀገሪቱ የውጭ ጉዳይና ዓለም አቀፍ ትብብር ሚኒስቴር ባወጣው መግለጫ አዲስ አበባና ካርቱም ከሰሞኑ በስፋት እየተወራ ያለውን የድንበር ላይ ውዝግብ በሰላማዊ መንገድና በንግግር መፈታት አለበት ብሏል፡፡ ሁለቱ ሀገራት ለቀጣናዊ መረጋጋትና ብልጽግና ትልቅ ሚና እንዳላቸው የጠቀሰው መግለጫው የተፈጠረውን ችግር በንግግር መፍታት አስፈላጊ ነው ብሏል፡፡ ዩኤኢ በሱዳን እና በኢትዮጵያ መካከል ያለው የድንበር ግጭት መባባስ እንደሌለበት ገልጻ ሁለቱም ሀገራት ለምስራቅ አፍሪካ ቀጠና ሰላምና መረጋጋት አይነተኛ ሚና ስላላቸው የተፈጠረውን ነገር በሰከነ መንገድ ማየት አለባቸው ብላለች፡፡

ሀገሪቱ ባወጣችው መግለጫ ሱዳን እና ኢትዮጵያ ለንግግር ቅድሚያ በመስጠት ውይይት መጀመር እና ውጥረትን ማርገብ እንደሚገባቸው አሳስባለች፡፡ ሀገራቱ ትብብር እና አጋርነትን በማስቀደም ችግራቸውን መፍታት እንዳለባቸው ያመለከተው መግለጫው ሁለቱም ወገኖች ለንግግር ቅድሚያ መስጠት አለባቸው ብሏል፡፡

ባለፈው ሳምንት የደቡብ ሱዳኑ ፕሬዚዳንት ሳልቫኪር ማያርዲት ሱዳን ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን የድንበር ውዝግብ በሰላማዊ መንገድ ብቻ መፍታት እንዳለባት መግለጻቸው ይታወሳል፡፡

የኢትዮጵያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ ዛሬ በሰጡት ሳምንታዊ ጋዜጣዊ መግለጫ “የሱዳን ኃይል በተጠናከረ ሁኔታ ወደ ኢትዮጵያ ግዛት የመግፋት እና ወደ ውስጥ ዘልቆ የመግባት እንቅስቃሴ እያሳየ ነው ያለው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ድንበሩ እስኪካለል ድረስ ነባራዊው ሁኔታ ባለበት እንዲቆይ (ሁለቱም ሀገራት በነበሩበት እንዲቆዩ) እ.ኤ.አ በ 1972 ስምምነት ተደርሶ እንደነበር ያነሱት ቃል አቀባዩ ፣ የአሁኑ የሱዳን ድርጊት ይህን ስምምነት የሚጥስ እንደሆነ ዛሬ በመግለጫቸው ጠቅሰዋል፡፡ አምባሳደር ዲና እንዳሉት ፣ ሱዳን ጦሯን አሰልፋ ወደ ኢትዮጵያ ግዛት መግፋት የጀመረችው ኢትዮጵያ በትግራይ ክልል በጀመረችው የሕግ ማስከበር ዘመቻ ምክንያት በሀገራቱ ድንበር ላይ የሳሳ የመከላከያና የጸጥታ ሁኔታ በመኖሩ ነው ብለዋል፡፡