በቤንሻንጉል ጉሙዝ የክልል፣ በመተከል የዞንና የወረዳ አመራሮች ለፍርድ መቅረብ አለባቸው

በመተከል ዞን በተከሰተው የፀጥታ ችግር ውስጥ እጃቸው ያለባቸውና በቸልተኝነት ኃላፊነት በአግባቡ ባልተወጡ ከክልል እስከ ወረዳ ያሉ አመራሮች ህጋዊና ፖለቲካዊ እርምጃ ተወስዶባቸዋል። የሚሉ ዘገባዎች ከመንግስት የመገናኛ ብዙሃን እየሰማን ነው።
እነዚህ እርምጃ የተወሰደባቸው በተለይ የስልጣን ሽግሽግ ተደርጎላቸው በመንግስት ወንበር ላይ እንዲቀመጡ የተደረጉት ባለስልጣናት በቤንሻንጉል ለተከሰተው የጸጥታ ችግር መግደልና ማፈናቀል ሚና ሲጫወቱ የነበሩ መሆኑን ካሁን ቀደም ሰምተናል። ባለስልጣናቱ በተለይ በፖለቲካው መስክ የጸጥታና ደሕንነት ባለስልጣናት የክልሉ ሰላም ደፍርሶ ዜጎች ላይ ሰቆቃ እንዲፈጸም ወንጀል ሲሰሩ እንደነበር በተደጋጋሚ መረጃዎች እና የአከባቢው ነዋሪዎች ጠቁመዋል።
የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልልና የመተከል ዞን እንዲሁም ወረዳዎች አመራሮች ተነስተዋል መባሉ መልካም ነው። ይሁንና አብዛኛዎቹ በሕግ መጠየቅ ያለባቸው ናቸው። እንደ አበራ ባያታ የመሳሰሉት ሰዎች በርካታ ጭፍጨፋዎች ላይ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ እጃቸው አለበት የሚባሉ ሰዎች ከአንዱ ስልጣን ወደሌላኛው መዘዋወር ሳይሆን ለፍርድ ነው መቅረብ ያለባቸው!
ችግሩን በመፍታት ማስተማር ካስፈለገ በቤንሻንጉል ጉሙዝ የክልል፣ በመተከል የዞንና የወረዳ አመራሮች ለፍርድ መቅረብ አለባቸው።
በሌላ በኩል መተከል ዞንና ወረዳዎች ላይ አመራር ሲነሳ፣ ሕዝቡን በሚወክል መልኩ እንጅ ሕዝብን በሚያስጠቃው አሰራር መሰረት አመራር ይተካ ከተባለ መፍትሔ ሊሆን አይችልም። ትልቁ መፍትሔ ሕዝቡ ተገቢውን ውክልና እንዲያገኝ ማድረግ በመሆኑ አንዱን አንስቶ ዝም ብሎ በቆየው አሰራር ሌላውን መተካት አይደለም።
መንግስት እነዚህን እርጉም ባለስልጣናት በቀጥታ ሕግ ፊት አቅርቦ መቅጣት ይኖርበታል። ባለስልጣናቱ ካልተቀጡና አከባቢው ላይ የፖለቲካ መፍትሔዎች ካልተወሰዱ ትላንት ሲፈጸም የነበረው ወንጀል ላለመደገሙ ዋስትና የለም። #MinilikSalsawi