በመጭው አገራዊ ምርጫ ጋር የኮሮና ተዋሕሲ ወረርሽኝ ስጋት መደቀኑ ተሰምቷል።

እንደሌሎች ሐገራት ምርጫዎች ሊራዘም ይችላል የሚል ግምት አለ።
ዓለም አቀፉ የዲሞክራሲ እና የምርጫ ድጋፍ ኢንስቲትዩት (IDEA) ባለፈው ሳምንት ባወጣው መረጃ መሰረት ወረርሽኙ በ21 ሀገራት ሊካሄዱ የነበሩ ምርጫ ነክ ሁነቶች ላይ ጉልህ ተጽዕኖ በማሳደሩ ለሌላ ጊዜ እንዲተላለፉ አስገድዷል።በበርካታ ሀገራት በፍጥነት የተስፋፋው የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ በየሀገራቱ ሊካሄዱ ቀን ተቆርጦላቸው ለነበሩ ሁነቶች መስተጓጎል ምክንያት ሆኗል።
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድም የኮሮና ቫይረስ ወረርሽኝ “በመራጮች ትምህርት፣ የምርጫ አስፈጻሚዎች ስልጠና እና የቁሳቁስ ስርጭትን” ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድር እንደሚችል ባለፈው ሳምንት መጨረሻ አስታውቋል።
በእነዚህ ተግባራት ላይ የሚደርስ መስተጓጎል በምርጫ የጊዜ ሰሌዳው ላይ ቀጥተኛ ተጽእኖ ኧእንደሚኖረው መገለጹ ይታወሳል። ከታች የሚመለከቱት ምስላዊ መረጃ በኮሮና ቫይረስ ሳቢያ የምርጫ ሁነቶቻቸውን ያራዘሙ የ10 ሀገራትን ሁኔታ ያሳያል።
ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ በሰጡት መግለጫ የኮሮና ቫይረስ ከተባባሰ በመጪው ምርጫ ዕጣ ፈንታ ላይ፤ የምርጫ ቦርድን ጥናት መሰረት አድርጎ፤ ውሳኔ እንደሚተላለፍ ተናግረዋል። ውሳኔው የሚገለጸው “የጋራ ስምምነት” ከተደረሰበት በኋላ ነው ብለዋል። “በቻይና እንዳየነው አይነት በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሄንን ጉዳይ መቆጣጠር፣ ማለፍ የሚቻል ከሆነ በአሰብነው እቅድ መሰረት መሄዱ ተመራጭ ቢሆንም ምናልባት ለተራዘመ ጊዜ ችግሩ የሚቀጥል ከሆነ እና ምርጫ ቦርድ ስራውን መከወን የሚቸገር ከሆነ፤ በሚያደርጉት ጥናት መሰረት ውይይት የሚደረግ ይሆናል” ብለዋል ጠቅላይ ሚኒስትሩ።
የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ የኮሮና ቫይረስ ለሳምንታት አሁን ባለበት ሁኔታ ከቀጠለ በምርጫ ኦፕሬሽን ላይ ተጽዕኖ ሊያሳድር እንደሚችል ማረጋገጫ ሰጥቷል። ምርጫ ቦርድ በቫይረስ ምክንያት ተጽዕኖ ሊደርስባቸው ያላቸው “ከፍተኛ የሰው ዝውውር ያሳትፋሉ” በሚል የገለጻቸውን “የመራጮች ትምህርት፣ የምርጫ አስፈጻሚዎች ስልጠና እና የቁሳቁስ ስርጭትን” ነው።