የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት አቅም አልባ ሆኛለሁ እያለ ነው።

የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ፈተና ውስጥ ወድቄያለሁ እያለ ነው።

ገዢው ፓርቲን ጨምሮ ከ100 በላይ የፖለቲካ ፓርቲዎች የፖለቲካ ሂደቱን ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ ለማድረግ የሚረዳቸው የቃል ኪዳን ሰነድ አዘጋጅተው መፈራረማቸው ይታወሳል ፡፡

ሰነዱ ለፊርማ የበቃው እልህ አስጨራሽ አንዳንዴም ፈታኝ ክርክሮች ተደርገውበት መሆኑን በውይይቱ ላይ ተገኝተው የነበሩ የፖለቲካ ፓርቲዎቹ መሪዎች ይናገራሉ ፡፡

በሰነዱ ላይ እንደተጠቀሰው ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት መገንባት የሚቻለው ‹‹በእኔ አውቅልሀለሁ›› መርህ ብቻ ሳይሆን ህዝቡ አምኖና ፈቅዶ ሲስማማበት ብቻ እንደሆነ ሁሉም ፓርቲዎች አምነውበታል ፡፡

ይህ ደግሞ ለሂደቱ በጣም አስፈላጊ የሆነ የመጀመሪያ እርምጃ ነው ይላሉ የፓለቲካው ሊሂቃን። ሁሉም የፖለቲካ ሀሳቦች በተቻለ መጠን በነጻነትና በእኩልነት እንዲወዳደሩ እድል እንዲሰጥ ሆኖ በሕግም በመዋቅርም ታግዞ ይዘጋጅል ፡፡

የአሰራሩ መጣስ አንድን ተጎጂ ድርጅት ብቻ የሚጎዳ ሳይሆን አጠቃላይ የስርዓቱን መሰረት ሊያናጋው እንደሚችል ታምኗል ፡፡

ስለሆነም ሰነዱ የዴሞክራሲያዊ ስርዓትን መሰረታዊ ያሰራር መርህ ድርጅቶቹ ሁሉ በጋራ መቀበላቸውና ለትግበራውም በቁርጠኝነት መቆማቸውን ያሳያል ፡፡

ይሁን እንጂ እነዚህና ያልዘረዘርናቸው ጠቃሚ ነጥቦች የተካተቱበት ይህ ሰነድን እንዲመራ የተቋቋመው የጋራ ምክር ቤት ፈተና ውስጥ መውደቁን ይናገራል፡፡

ሲቋቋም ወሳኝ አቅም እንዲኖረኝ ታስቦ ቢሆንም በገንዘብ እጦት እግር ከወርች ታስሪያለሁ ነው የሚለው ፡፡

የፋይናስ ችግሩን ለመቅረፍና የተቋቋመበትን ዓላማ ወደ መሬት ለማውረድ ከምርጫ ቦርድ እስከ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተደጋጋሚ ጥያቄ ማቅረቡን ገልጿል ፡፡

ምክንያቱም ገዥው ፓርቲን ወክለው ፊርማቸውን ያኖሩት እርሳቸው ስለነበሩ ፡፡ምን ያደርጋል ፊርማቸው ሳይቀደርቅ አቅም አልባ ሆኛለሁ ነው የሚለው፡፡

ኤትዮ ኤፍ ኤም ከምክር ቤቱ ዋና ሰብሳቢ አቶ ሙሳ አደም ጋር በነበረው ቆይታ ምክር ቤቱ በፓርቲዎች መካካል የሚነሱ ችግሮችን ለመፍታት እንኳን መቸገሩን ሰምቷል ፡፡

እስካሁን ከ15 የበለጡ መፍትሔ እንሻለን ባይ ጠያቂ ፓርቲዎች ጥያቄያቸውን አቅርበዋል፤ ይሁን እንጂ አሁንም ችግሩ በሼልፍ ላይ ያለ ነው፡፡

ይህ የቃልኪዳን ሰነድ በመንግሥት አስገዳጅነት የተዘጋጀ አይደለም የሚሉት አቶ ሙሳ በኔ አመለካከት ግን ሕግ ሆኖ ከመውጣቱም በላይ ፋይዳ አለው ። ይህ የቃል ኪዳን ሰነድም በሁሉም ዘንድ የሞራል አስገዳጅነት እንዲኖረው፤ ሕግን ፈርቶ ሳይሆን የምንፈልገውን ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ለመመስረት በዚህ ሰነድ ውስጥ በተቀመጡት ስርዓቶች መሰረት ብቻ ፓርቲዎቹ በፍላጎታቸው መስማማታቸው ነው ትልቁ ፋይዳው ሲሉም ያክላሉ።

አባሎቻቸውና ደጋፊዎቻቸው በዚህ የጋራ የሞራል እሴት ማነጽ ከተቻለ ወደ ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ምስረታ የምናደርገውን ጉዞ የዚያኑ ያክል የሚያቀል ነበር ባይ ናቸው፡፡

የኢትዮጲያ ምርጫ ቦርድ የኮሚኒኬሽን ጎዳዩች አማካሪ ወ/ሮ ሶሊያና ሽመልስ “የጋራ ምክር ቤቱ ገለልተኛ ሆኖ እንደ መስራቱ የፓለቲካ ፓርቲዎቹም የራሳቸውን ድጋፍ ማድረግ ይገባቸዋል”ይላሉ፡፡

የጋራ ምክር ቤቱ ከዚህ ቀደም የገንዘብ እጥረት እንዳለበት አላሳወቃችሁም ወይ ምንስ ምላሽ ሰጣችሁ ስንል ላነሳንላቸው ጥያቄ እንዲህ ብለዋል፡፡

“በፓርቲዎች የቀረበ አቤቱታ አለ፡፡ ማጣራት አለብን እና ገንዘብ ያሰፈልጋል ብለዋል፡፡እኛም አቤቱታዎቹ አንድ በአንድ ይቅረቡና እንደ አንገብጋቢነታቸው ተመልክተን እንፈታለን ብለናል፤

ይሁን እንጂ የጋራ ምክር ቤቱ በደፈናው ለሶስት ወራት የሚሆን 3 ነጠብ 8 ሚሊየን ብር የጠየቀውን ልንመልስ አንችልም ምክንያቱም እኛ በዚህ ልክ ገንዘብ የለንም” ብለዋል፡፡

በፓርቲዎች ቁጥር ልክ እንዲያምውም በሚበልጥ ሆኔታ የፓርቲዎችን ችግር ይፈታል ተብሎ ተስፋ የተጣለበት ይህ የጋራ ምክር ቤት፣ የመጀመሪያው የስልጣን ዘመኑን አጠናቆ ለተከታዮቹ ወራት የሚዘልቁ መሪዎችን ለመተካት ሽር ጎድ ላይ ነው ያለው፡፡

አይቀሬ ነው የተባለው ምርጫም እነሆ ደረስኩ ደረስኩ እያለ ነው፡፡

ETHIO FM 107.8