ይድረስ ለአቶ ልደቱ አያሌው፣ ለምን አምርሬ እጠላህ እንደነበረም ዛሬም ድረስ በቅጡ አይገባኝም – እያሱ እንድሪስ ተሰማ

ይድረስ ለአቶ ልደቱ አያሌው ።

እንደ ልጅነቴ ማንዴላ ብዬ እጄን ደም እስኪያግት ድረስ ባላጨበጭብልህም ተጨማሪ ዕድል ያሻሃል ። ከማንም የከፋህ ሴይጣንም አይደለህም ፣ ቢያንስ ቢያንስ እንደ ሌሎቹ ሁሉ ሌላ ፓስፖርትና በኢትዮጵያ አንድነት ላይ የምትቆምረዉን ሴራ ከአሉባልታ ዉጪ አልሰማሁም ።

እዉነት ለመናገር ለምን አምርሬ እጠላህ እንደነበረም ዛሬም ድረስ በቅጡ አይገባኝም ነበር። “የእርሻ ዉስጥ አረም” የሚለዉን መፅሃፍህን ራሱ ከሰዉ ተዉሼ አቃጥዬዉ እንደነበረ ሁሉ አስታዉሳለሁ። ምናልባትም ምክንያት አልባነት ሳይሆን የተጫንነዉ ሶፍትዌር በልካችን የተሰፋ ስለነበር ይመስለኛል።

ወንበር ለመደርደር መጥቶ ፖለቲከኛ የሆኑ እስካርቭ ጠምጣሚ አያሌ መንደርተኞችና ጭራ ለምኔ ሰዎች ፖለቲካዊ አቅማቸዉ ድንኮች “ፒግሚ” የሆኑ ስምህን ሲያከፋፉት ሰምቼያለሁ ።

ሀጥያትህን ለሚሰርይልህ አምላክ እንተወውና ። እስቲ ፃድቃኖቹ ነቢያት ነን ባዮቹ የመጀመሪያዉን ድንጋይ ሲወረዉሩ እንያቸዉ ??? መልሱን አሳምረዉ ያዉቁታል። በመስታዉት ቤት ያለ ሰዉ ድንጋይ ወርዉሮ “እንደርቢ” አይጠራም። ትርፉ -ዉሃ- መረጫጨት ነዉ ።

በግሌ የዛኛዉን ዘመን የ”ቸ” እና የ” ሸ” ሴረኞች ቩቩዜላ አልሆንም ፣ በተለይም ያችን ካባና ለምድ ገፈዉ እስካልጣሉ ድረስ ፣ የማንም ቲፎዞ መሆን አልፈልግም ።

በመጨረሻም የገባኝ ነገር የዛን ዘመን የፖለቲካ ጀብራሮች የሴራቸዉን ክህሎት እና የካበተ ልቀት ነዉ ። ለምን እንደዚህ እንደሚፈሩህም ጭምር የተከሰተልኝ ደግሞ ዘግይቶ ነዉ።

ዛሬ ትላንትና አይደለም ። እንደ ሆሞ ሳፒያንስ ዘመን በጋርዮሽ ልጓም አንሰተርም። በደቦ ዉደዱ ጥሉ የሚባል ትናንሽ ነገስታቶች በጫንቃችን የሉም።

ሲጀመር ፖለቲካን ለፅድቅ ብለህ አልጀመርክም።  “ኤጲስ ቆጶስም” አይደለህምና ከአንተ ቡራኬ መጠበቅም አልነበረብንም። ለሌላዉ ያልተነፈገዉን ይቅርታ ፣ ለምንና ለማን ብዬ እኔ ተራዉ ሰዉ እንዴት እነሳሃለዉ ? ማነዉ ንፁህ ? ማነዉ ያልተዳራ ? ማነዉ በሕዝብ ዕንባ ላይ ያልሴሰነ ? እየተዋወቅን ።

በዚህም ተባለ በዚያ እኔን ጨምሮ ብዙሃኑ ኢትዮጵያዊ “በቅጡ ለማላዉቀዉ ሃጥያትህ ንሰሃ ” ለአምላክህ እስከገባህ ድረስ ፣ ዳግም አንተን የማልሰማበት ምንም አይነት ምድራዊ ምክንያት አይኖርም።

በነገራችን ላይ ከአዞ ለተሰራዉ ቆዳህና ፣ ለዝሆኑ ጆሮህ ባርኔጣዬን አንስቼያለሁ ይህንን ሳላደንቅ ባልፍ ሀኬት ይሆንብኛል ። Kudos !

There is no substitute for hard work. Never give up. Never stop believing. Never stop fighting.

እናም አቶ ልደቱ በአመንክበት መንገድ ቀጥል የሃገሬ ልጅ በርታ ! ቸሩ ሁሉ መልካሙ ሁሉ ይግጠምህ ።