ለምግብነት ሊውል የነበረ 16 ኩንታል ምንነቱ ያልታወቀና ለወፍጮ የተዘጋጀ ቁስ በቁጥጥር ስር ዋለ፤ መጠኑ በውል ያልታወቀ የተበላሸ በርበሬም ተይዟል፡፡
(አብመድ) በባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ዳግማዊ ምኒሊክ ክፍለ ከተማ ‹‹አቡነ ሐራ›› ተብሎ ከሚጠራው አካባቢ ከሚገኙ የእህል ወፍጮ ቤቶች በአንደኛው ለምግብነት የማይውልና ምንነቱ ያልታወቀ ቁስ ለመፈጨት እንደተዘጋጀ በቁጥጥር ስር ውሏል፡፡
በቁጥጥር ስር የዋለው ቁስም 16 ኩንታል ነው፡፡ ይህ በዓድ ቁስ ተፈጭቶና ከሌሎች የምግብ እህሎች ጋር ተቀላቅሎ ለምግብነት እንዲውል ታስቦ የተዘጋጀ መሆኑን ፖሊስ አስታውቋል፡፡
የባሕር ዳር ከተማ አስተዳደር ፖሊስ መምሪያ ኃላፊ ኮማንደር ዋለልኝ ዳኘው እንደገለጹት ባዕድ ቁሱ በኅብረተሰቡ ጥቆማ ዛሬ ከቀኑ 9፡30 በቁጥጥር ስር ውሏል፡፡
ከወፍጮ ቤቶቹ አቅራቢያም ለአገልግሎት ሊውል የማይችል የተበላሽ በርካታ ኩንታል በርበሬ በቁጥጥር ስር ውሏል፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች ለአብመድ እንደተናገሩት ከዚህ ቀደም የተበላሸው በርበሬ አገልግሎት ሊሰጥ ከሚችል በርበሬ ጋር ተደባልቆ ሲዘጋጅ ተመልክተዋል፡፡ ስለ ሕገ-ወጥ ድርጊቱ ለሚመለከተው አካል በተደጋጋሚ አሳውቀው እንደነበርም ተናግረዋል፡፡
እንደ ኮማንደር ዋለልኝ ገለጻ እንደዚህ ዓይነት ሕገ-ወጥ ድርጊቶች በባሕር ዳር ከተማ ያልተለመዱ ናቸው፡፡
በኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድኃኒት ቁጥጥር ባለስልጣን የሰሜን ምዕራብ ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት ኃለፊ አቶ ሙሉጌታ ቆየ ደግሞ እንደዚህ ዓይነት በዓድ ነገሮች በአጭር እና በረዥም ጊዜ በሰዎችን ላይ የጤና ጉዳት እንደሚያደርሱ ተናግረዋል፡፡