በመጠለያዎች ውስጥ በአንድ ወር 118 ሴቶች ወልደዋል

ከሰሜን ወሎ ዞን አካባቢዎች በጦርነት ምክንያት የተፈናቀሉ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ዜጎች በተለያዩ በደሴ እና ኮምቦልቻ መጠለያ ጣቢያዎች፣ ሌሎች ቁጥራቸው በውል የማይታወቅ ደግሞ በየዘመዶቻቸው ቤት ተጠልለው ይገኛሉ።

እነዚህ ተፈናቃይ ወገኖች ረሃብን ጨምሮ ለተለያዩ የጤናና የደኅንነት ችግሮች ተጋልጠዋል።

በሰሜን ወሎ ዞን የስልክም ሆነ የኢንተርኔት አገልግሎት በመቋረጡ አሁን ያለውን ሁኔታ ለማወቅ አስቸጋሪ ሆኗል።

በአሁኑ ጊዜ በደሴ ከተማ 14 የተፈናቃዮች የመጠለያ ካምፖችና ትምህርት ቤቶች እነዚህን ተፈናቃዮችን እያስተናገዱ ነው።

በካምፖቹ ውስጥ ከህጻን እስከ አዋቂ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች ተጠልለው የሚገኙ ሲሆን፣ ከእነዚህ ውስጥም በርካታ ህጻንት፣ ወላድና ነፍሰጡር እናቶች ይገኛሉ።

የሰሜን ወሎ ዞን የጤና መምሪያ ለ ቢቢሲ በሰጠው ቃል በመጠለያዎች ውስጥ ባለፈው 1 ወር ብቻ ቢያንስ 118 ሴቶች ወልደዋል።

በሰሜን ወሎ ዞን ከጦርነቱ በፊት 6 ሆስፒታሎች በርካታ የግል የጤና ተቋማትና ጤና ጣቢያዎች ለእናቶች የወሊድ አገልግሎትና ክትትል ይሰጡ ነበር።

እንደመምሪያው ገለፃ ፥ ህወሓት አካባቢዎቹን ከተቆጣጠረ ወዲህ የጤና ተቋማቱ ሙሉ በሙሉ በመውደማቸውና እናቶች በዚህ ወቅት ምን እንደገጠማቸው አይታወቅም።

ከወላድ እናቶች በተጨማሪም በዞኑ ውስጥ የተለያዩ መድኃኒቶችን ይወስዱ የነበሩ ሕሙማን ሕክምናቸው በመቋረጡ አሁን በሕይወት ይኖራሉ ለማለት እንደሚያስቸግርም የጤና መምሪያው ገልጿል።

ሰሜን ወሎ ዞን ፦
-ከ18 ሺ በላይ የስኳር ታካሚዎች፣
-ከ20 ሺ በላይ የፀረ ኤችአይቪ መድኃኒት ተጠቃሚዎች፣
-1145 የቲቢ ታካሚዎች ነበሩ፤ አሁን ያሉበት ሁኔታ አይታወቅም።