ጁንታው መቃብር ፈንቅሎ ሊወጣ አይችልም፤ ራሱ በለኮሰው እሳት ተለብልቦ ጠፍቷል – ሜ/ጄኔራል መሐመድ ተሰማ

ጁንታው በዋሻ ውስጥ ሆኖ የትግራይን ህዝብ ለማደናገር የሚያደርገው ጥረት እንደማይሳካ የአገር መከላከያ ሰራዊት ገለፀ።

የአገር መከላከያ ሰራዊትን ስም በማጥፋት ህዝብን ብዥታ ውስጥ ለመክተት የሚንቀሳቀሱ መገናኛ ብዙሃንን በህግ እንደሚጠይቅም አስታውቋል።

የመከላከያ ኢንዶክትሪኔሽን ዋና ዳይሬክተር ሜጀር ጄኔራል መሐመድ ተሰማ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለኢዜአ መግለጫ ሰጥተዋል።

ሜጀር ጄኔራል መሐመድ በመግለጫቸው አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ህወሓት የተባለ ድርጅት መሬት ላይ እንደሌለ አመልክተዋል።

“ጁንታው መቃብር ፈንቅሎ ሊወጣ አይችልም፤ ራሱ በለኮሰው እሳት ተለብልቦ ጠፍቷል” ብለዋል።

ይሁን እንጂ ተበታትነውና በዋሻ ውስጥ ተደብቀው የሚገኙ የጁንታው ትርፍራፊዎችና ከፍተኛ ተከፋይ አክቲቪስቶቻቸው አሁንም የሐሰት ወሬ እየነዙ ይገኛሉ ነው ያሉት።

የጁንታው ቃል አቀባይ የነበረው ጌታቸው ረዳ ከሰሞኑ በስልክ አስተላለፈው ተብሎ የወጣው መልዕክት የትግራይ ወጣቶችን ለማደናገር የተደረገ ነው ሲሉ ገልጸዋል።

የቀሩትን የጁንታ ቡድን አባላት ከተደበቁበት ጉድጓድ ለማውጣት የአገር መከላከያ ሰራዊት ከፍተኛ ርብርብ እያደረገ ነው ያሉት ሜጀር ጄኔራል መሐመድ ተሰማ ጁንታውን የማደንና ሰላም የማስከበሩ ተግባር ተጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል። EBC