ሱዳን ብሉናይል ግዛት ድረስ ስልጠና የሚሰጣቸው የመተከል ታጣቂዎች እንዳሉ መንግስት እያወቀ ፀጥ ብሏል

መተከል የሰቆቃ ምንጭ ራሱ የመንግስት መዋቅሩ እንደሆነ የቢሻንጉል ጉምዝ የምክርቤት አባል ተናገሩ፡፡
አሻራ – አቶ ካሳሁን አዳነ የተባሉ የመተከል ዞን ወኪል ለአማራ ቴሌቬዥን እንደተናገሩት የመተከል የዘር ጭፍጨፋ መንስኤው ራሱ መንግስት ነው ብለዋል፡፡ የተከበሩ አቶ ካሳሁን ለአማራ ቴሌቬዥን እንደተናገሩት ሱዳን ብሉናይል ግዛት ድረስ ስልጠና የሚሰጣቸው ታጣቂዎች እንዳሉ መንግስት እያወቀ ፀጥ ብሏል ብለዋል፡፡
የኦነግ ሀይል በካማሺ ዞን በኩል እንደገባ ለኮማንድ ፓስቱ መረጃ ደርሶትም መፍትሄ መስጠት አልቻለም ነበር፡፡ እስካሁን በሁለት ሳምንት ውስጥ ብቻ ከ400 በላይ ንፁሃን በገፍ ተጨፍጭፈው በሴኖትራክ እየተጫኑ በጫካ ተቀብረዋል፡፡ ኮማንድ ፓስቱም ለአምስት ወር ያህል ተረጋግቷል እያለ ያፌዛል፡፡ መተከል በኮማንድ ፖስት መተዳደር የጀመረው ከመስከረም ጀምሮ ነበር፡፡ ኮማንድ ፓስቱ ግን ቀባሪ እንጂ አዳኝ አልሆነም፡፡ 200ሺ ሰው ሲፈናቀል ኮማንድ ፖስቱ አብሮ አለ፡፡ ትናንትናም 180 ሰው ሲሞት ኮማንድ ፓስቱ የደረሰው ለቀብር ነው፡፡
ይህ ያበሳጫቸው ወገኖች ብሄራዊ የሀዘን ቀን እንዲታወጅ እየወተወቱ ሲሆን፣ ህዝብ ማዳን ያልቻሉ አመራሮች እንዲጠየቁ እስከ ተባበሩት መንግስታት ድርጅት ድረስ እያደራጁ እንደሆነ አሻራ ሰምቷል፡፡መንግስታዊ ግድያዊ እስካልቆመ ድረስ ልዮ ልዮ የመፍትሄ እርምጃዎች እንዲወሰዱ እየተጠየቀ ነው፡፡ መንግስት ግን በራሱ ሚዲያ ቅዱስ ሆኖ ይቀርብና በተግባር የረከሰ ስራ መስራቱን ቀጥሎበታል፡፡
እስካሁን በመተከሉ ጅምላ ጭፍጨፋ ይፋ መግለጫ ካለመሰጠቱ በላይ አጀንዳ ፈልገን ጭፍጨፋውን እናዘናጋ የሚል ውይይት በካድሬዎች እንደተጀመረ እየተሰማ ነው፡፡ ህዝቡን በደራሽ አጀንዳ እየጠመዱ መተከልን የደም እርሻ እያደረጓት ቀጥለዋል፡፡ የአሻራ አስተያየታቸውን የሰጡ ወገኖች” የአማራ ብልፅግናም በጉዳዮ ዙሪያ የቀድሞ ፉከራው የት እንደጠፋበት ግራ አጋቢ ነው ብለዋል፡፡”
የኮማንድ ፓስቱ አሁንም አስከሬን ስርቆ ውስጥ መጠመዱን የመተከል ምንጮች ነግረውናል፡፡ ኮማንድ ፓስቱ ዛሬም ማስተባበያ የሰጠ ሲሆን፣ አመራር ለውጫለሁ ያላቸው እና በጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጠና የወሰዱት የመተከልን ችግር የመፍታት የሞራልም ሆነ የእውቀት ችግር እንዳለባቸውም እየተነገረ ነው፡፡