የዳግማዊ አፄ ምኒልክ መታሰቢያ ሙዚየምና የባሕል ማዕከል ተመረቀ

የዳግማዊ አፄ ምኒልክ መታሰቢያ ሙዚየምና የባሕል ማዕከል ተመረቀ

(ኤፍ ቢ ሲ) የዳግማዊ አፄ ምኒልክ መታሰቢያ ሙዚየምና የባሕል ማዕከል በጥንታዊቷና ታሪካዊቷ ከተማ አንኮበር ተመረቀ፡፡

የወረዳው ባሕልና ቱሪዝም ጽህፈት ቤት ሓላፊ ፈለቀ ምሕረት እንደተናገሩት÷ አንኮበር ጥንታዊ የብራና መጻሕፍት፣ የወርቅ ጽናጽል፣ የብር ከበሮ እና መቋሚያን ጨምሮ በወቅቱ የነገሥታቱ መገልገያ የነበሩ በርካታ ታሪካዊ ቅርሶች መገኛ ናት።

ነገር ግን እነዚህን ቅርሶች በተደራጀ ቦታ ለማስቀመጥና ለጉብኚ ክፍት አልነበሩም ያሉ ሲሆን የተቀመጡትም በወረዳው በሚገኙ 97 ጥንታዊ አብያተ ክርስቲያናት ተበታትነው ነበር።

በዚህም ምክንያት ቅርሶችን ከነታሪካቸው በሚፈለገው ደረጃ ለትውልድ ማስተዋወቅ አልተቻለም ብለዋል።

በዚህም ወረዳውም በቱሪዝም ተጠቃሚ መሆን አልቻለም ነው ያሉት።

እንደ ኃላፊው ገለጻ ወረዳው ለቤተ መዘክሩ ግንባታ ከ6 ሚሊየን ብር በላይ ወጪ ያደረገበት ሲሆን ቤተ መዘክሩ የደኀንነት ካሜራዎች ተገጥመውለታል።

የክልሉ መንግሥትም ወደ 259 ሺህ ብር መድቦ ቅርሶች ከሰው ንክኪ ነፃ ሆነው እንዲጎበኙ የሚያስችል መስተዋት አሠርቷል።

ይህም ቅርሶች ለጉብኝት ክፍት እንዲሆኑ ከማስቻል ጀምሮ ደኀንነታቸው በአስተማማኝ መልኩ እንዲጠበቅ ያደርጋል እንዲሁም የወረዳውን የቱሪዝም እንቅስቃሴም በከፍተኛ ደረጃ ያነቃቃል ተብሎ ታምኖበታል።

እንደ አብመድ ዘገባ ወረዳውም ቱሪዝሙን ይበልጥ ለማነቃቃት በቤተ መዘክሩ አጠገብ ደረጃውን የጠበቀ የእንግዶች ማረፊያ ለመገንባት እንቅስቃሴ መጀመሩ ታውቋል፡