በትግራይ ክልል ከትናንት ሌሊት ጀምሮ የኢንተርኔትና የስልክ አገልግሎት መቋረጡ ተገልጿል።

በትግራይ ክልል ከትናንት ሌሊት ጀምሮ የኢንተርኔትና የስልክ አገልግሎት መቋረጡ ተገልጿል።

BBC Amharic : በኢንተርኔት ነፃነት ላይ የሚሰራው ኔት ብሎክስ የተሰኘው ድርጅትም ከዛሬ ዕለት ጥዋት ጀምሮ ኢንተርኔትና የስልክ አገልግሎት መቋረጡንም አስታውቋል።

በአሁኑ ሰዓት የትግራይ ክልል ቴሌቪዥንም ሆነ ድምፂ ወያነ የሚሰሩ ሲሆን የተለመደ ፕሮግራማቸውን እያስተላለፉም ይገኛሉ።

ከትናንት አመሻሽ ጀምሮ በትግራይ ክልል ውስጥ በአንዳንድ አካባቢዎች የፀጥታ ኃይሎች ሲንቀሳቀሱ እየታየ የነበረ መሆኑ የተገለፀ ሲሆን በዛሬው እለት ጠቅላይ ሚኒስትር ዐብይ አህመድ ክልሉን በሚያስተዳድረው ሕወሃት ላይ ጦርነት መከፈቱን አስታውቀዋል።

ጠቅላይ ሚንስትሩ በአገሪቱ ብሔራዊ ቴሌቪዥን ጣቢያ ቀርበው የመከላከያ ሠራዊት በኮማንድ ፖስት እየተመራ “ሀገሩን የማዳን ተልዕኮውን እንዲወጣ ትእዛዝ ተሰጥቶታል” ብለዋል።

ትናንት ሌሊት (ጥቅምት 24/ 2013 ዓ.ም) ወደ አምስት ሰዓት አካባቢ በመቀሌና አስራ አንድ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ኩዊሃ ከፍተኛ የተኩስ ድምፅ ይሰማ እንደነበር የቢቢሲ ዘጋቢ ከስፍራው አድርሷል።

እስካሁን ድረስ ከትግራይ ክልል በኩል ምንም አይነት መረጃ ያልተገኘ ሲሆን የህወሃት ከፍተኛ አመራር ጌታቸው ረዳ ትናንት ሌሊት “ወንድምና እህቶች ተረጋጉ” በማለት በፌስቡክ ገፃቸው አስፍረው ነበር።