የጠ/ሚ አብይን የአሜሪካ ጉዞ ለማደናቀፍ አምባሳደር ካሳ ተክለብርሃንና ግብረአበሮቹ የሸረቡት ሴራ (መሳይ መኮንን)

የዶ/ር አብይ አህመድን የአሜሪካን ታሪካዊ ቆይታ ለማሰናከል አንድ ሃይል ጉልበት ያገኘ ይመስላል። በዋሽንግተን ዲሲና በሎስአንጀለስ ዝግጅቱን በበላይነት የሚመሩት አፍቃሪ ህወሀቱ ካሳ ተ/ብርሃንና ብርሃኔ ኪዳነማርያም ናቸው። ይህን ታሪካዊ ጉብኝት በእነዚህ የህወሀት ወኪሎች እንዲመራ መደረጉ ዋጋ ሊያስከፍል ይችላል።

ታማኝ በየነን ከመርሃ ግብሩ የሰረዘው ኤምባሲው ነው። ካሳ ተክለብርሃን የኮንቬንሽን ማዕከሉን መድረክ እመራለሁ ብሎ የታማኝን ቦታ አስለቅቋል። ስለኤችአር 128 ማብራሪያ ለመስጠትና ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥያቄ ለማቅረብ ፕሮግራም የተያዘላቸው ዲያቆን ዮሴፍ ተፈሪም በመጨረሻው ሰዓት ምንም ዓይነት ንግግር እንደማያደርጉ በኤምባሲ በኩል በተላለፈ ትዕዛዝ መሰረዙ ተሰምቷል። የዲያስፖራው ድምፅ እንዲታፈን በካሳና ግብረአበሮቹ እየተደረገ ያለው ስውር ዘመቻ እየተሳካላቸው ነው።

ካሳ ተክለብርሃን በአፉ ጤፍ ሲቆላ፣ ሲያታልል ቆይቶ ባለቀ ሰዓት ያደፈጠበትን መረብ ዘርግቷል። እየተጣጠፈ በብልጣብልጥ ተራ የማታለል እንቅስቃሴው ውስጥ ቆይቶ መሰሪ ባህሪውን ከሸለፈቱ በመፈልቀቅ በእኩይ ተግባሩ የዶ/ር አብይን ታሪካዊ ጉዞ እየበጠበጠው ነው።

እንደሰማነውም የ1500 ሰዎች የውይይት መድረክም በህወሀት ተጠልፏል። ካሳ መድረኩን በህወሀት ደጋፊዎች እንዲሞላ በጀርባ የግብዣ ጥሪዎችን በትኗል። የጠቅላይ ሚኒስትሩን ታሪካዊ ቆይታ ለማደብዘዝ የታቀደው የእነካሳ ሴራ ካልተሰበረ ችግር ሊገጥመው እንደሚችል ይገመታል።

ይህ አጋጣሚ እንዳይሰናከል የመስተንግዶው ኮሚቴ በቀረው ጊዜ ሁሉም የሚችለውን ማድረግ ይጠበቅበታል። የካሳ ሴራ መክሸፍ አለበት። ዶ/ር አብይ ይህን ሰው ዋሽንግተን ዲሲ ማስቀመጥ አልነበረባቸውም። ለቀጣይ አብዝተው ቢያስቡበት ጥሩ ነው።

በዋሽንግተን ዲሲ የበረከት ስምዖን ጀሌ አምባሳደር ካሳ ተከለብርሃን