ወዳጃችንን አቶ ኢሳያስ አፍወርቂን ስለሐገራቸው ኢትዮጵያ ሲሉ በኤርትራ የታሰሩ ኢትዮጵያውያን የጦር ምርኮኞች እንዲፈቱ እንጠይቃለን።

ወዳጃችንን አቶ ኢሳያስ አፍወርቂን ስለሐገራቸው ኢትዮጵያ ሲሉ በኤርትራ የታሰሩ ኢትዮጵያውያን የጦር ምርኮኞች እንዲፈቱ እንጠይቃለን። አቶ ኢሳያስ በኤርትራ የታሰሩ የጦር ምርኮኞች ቤተሰቦችን እምባ ሊያብሱ ይገባል።

በክቡር ጠቅላይ ሚኒስትራችን ዶክተር አብይ አሕመድና በክቡር የኤርትራው ፕሬዝዳንት ኢሳያስ አፈወርቂ መካከል ላለፉት ሃያ አመታት በአዲስ አበባና አስመራ መንግስታት መካከል የነበረውን የጦርነት ቁርሾ የሚያስወግድ አዲስ ምእራፍን የሚፈጽም ታሪካዊ የሰላም ስምምነት ተፈርሟል። የአስመራ ህዝብ ባለፈው ሳምንት ኤርትራ ለጉብኝት የሔዱትን ጠቅላይ ሚኒስትራችንን ለየት ሞቅ ደመቅ ያለ አቀባበል በማድረግ ትልቅ ፍቅሩንና ደስታውን ለግሷል። ክቡር አቶ ኢሳያስም ዶክተር አብይን እንደ ውጪ እንግዳ ሳይሆን እንደ ግል ጓደኛ ፍቅርና ናፍቆት የሰረፀበት ደማቅ አቀባበል አድርገውላቸዋል።አቶ ኢሳያስ አዲሱ የኢትዮጵያ አስተዳደር እንደተስማማቸው በተግባር አሳይተዋል።

የኤርትራው መሪና ባለስልጣኖቻቸው ከኢትዮጵያ ጋር የከፈቱት የሰላምና የፍቅር ምእራፍ ደስታን ሲያጎናፅፋቸውቅ እኛንም ትልቅ ሐሴት አስደርጎናል። ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ ወዳጃችንን አቶ ኢሳያስ አፍወርቂን ስለሐገራቸው ኢትዮጵያ ሲሉ በኤርትራ የታሰሩ ኢትዮጵያውያን እንዲፈቱ እንጠይቃለን። ስ
ለሃገራቸው ሲሉ በጦርነት ተሳትፈው የተማረኩ ምርኮኞችን የ ኤርትራ መንግስት ስለፍቅራችን ሲል ሊለቃቸው ይገባል። ስለ ኢትዮጵያ ሲሉ በ ኤርትራ እስር ቤቶች የሚገኙ ኮሎኔል በዛብህ ጴጥሮስ ፣ ኮሎኔል ታደሰ ሙሉነህ ፣ የፊልም ባለሙያው ዮሴፍ ሃይማኖትን ጨምሮ እጅግ በርካታ የጦር ምርኮኞች ሊለቀቁና ከቤተሰቦቻቸው ሊቀላቀሉ ይገባል። የኢትዮጵያውያንን ደስታ ሙሉ ለማድረግም ይህ ትልቅ የፍቅር መግለጫ ነው። ወይንም በእስር ቤት ሞተው ከሆነ ለቤተሰቦቻቸው መርዶ ሊነገር ይገባል።

በድንበር ጦርነቱ ወቅት ተማርከው የነበሩ ኤርትራያንን ሙሉ በሙሉ ኢትዮጵያ መልቀቋና ወደ ሃገራቸው መስደዷ ይታወሳል። የ ኤርትራ መንግስት ግን የጦር ምርኮኞችን እስከዛሬ ድረስ አለቀቀም። የፊታችን ቅዳሜ አዲስ አበባ የሚገቡት አቶ ኢሳያስ እስረኞችን እንዲፈቱ መልካም ፈቃደኝነት ሊያሳዩ ይገባል። አቶ ኢሳያስ በኤርትራ የታሰሩ የጦር ምርኮኞች ቤተሰቦችን እምባ ሊያብሱ ይገባል።