በቃል ሲነገረው ያልሰማ ህዝብ በመከራ ሊማር ወስኗል

ሚላን…ኒውዮርክ….ቀጥሎ አዲስአበባ
==============================
እሺ እባካችሁ…. የትላንቱ ገበያ እንዴት ነበረ? ዛሬስ አውዳመቱ እንዴት እያለፈ ነው? መልካም… ልክ የዛሬ ሁለት ወር (February 19/2020) በሰሜን ኢጣሊያ ሎምፓርዲ ግዛት Bergamo ከተማ የተመሠረተው የአትላንታ ክለብ ከስፔኑ ቫሌንሺያ ጋር ለአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ጨዋታ ነበራቸው። ከብዙ አመታት ጥበቃ በኋላ በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ የመጫወት ዕድል ያገኘው የአትላንታ ክለብ ደጋፊዎች ደስታቸው የተለየ ነበር። በቤርጋሞ ከተማ የሚገኘው ስታዲየም በቂ ባለመሆኑ በሚላኑ ሳንሴሮ ስታዲየም እንዲካሄድ ተወሰነ። ይህን ጨዋታ ለመመልከት የቤርጋሞ ከተማ ነዋሪዎች ነቅለው ሚላን ከተማ ገቡ። ከተወሰኑ ቀናት በኋላ በጨዋታው ከታደሙት 44ሺህ ተመልካቾች ውስጥ 40ሺህ የሚሆኑት ተመልካቾች በኮሮና ቫይረስ ተይዘዋል። ጨዋታውን የኢጣልያኑ አትላንታ ቫሌንሺያ 4 – 1 አሸነፈ። የአትላንታ ደጋፊዎች በደስታ ጮቤ ረገጡ፣ በደስታ ጨፈሩ፣ አንገት ለአንገት ተቃቅፈው የክለባቸውን መዝሙር ዘመሩ።
የአትላንታ እና ከቫሌንሺያ ጨዋታ በሚካሄድበት ዕለት (February 19/2020) ኢጣሊያን ውስጥ በኮሮና ቫይረስ የተያዙ ሰዎች ብዛት ሦስት ብቻ እንደነበር Wall Street Journal ዘገባ ያስረዳል። ከ20 ቀን በኋላ (March 10/2020) የቤርጋሞ ከተማ ነዋሪዎች እንደ ቅጠል ይረግፉ ጀመር። ከተጠቀሰው እግር ኳስ ጨዋታ ቀጥሎ ባሉት ጥቂት ቀናት ውስጥ በሚላን ከተማ አቅራቢያ ወደ 100 ሺህ የሚጠጋ ህዝብ የሚገኝበት ቬስትቫል ነበር። በሳንሴሮ ስታድየም በተካሄደው ጨዋታ ላይ እንደ እንኩቤተር የተፈለፈለው የኮሮና ቫይረስ በዚህ ቬስትቫል ላይ በከፍተኛ ፍጥነት ተስፋፋ። ከዚያ በኋላ የተጠቀሱት ቦታዎች በሚገኙበት በሰሜናዊ ኢጣሊያ የሚገኘው የሎምፓርዲ ግዛት ስንት ሺህ የኢጣልያ ዜጎች በገፍ እንደረገፉ ሁላችንም የአይን እማኞች ስለሆን ብዙም መናገር አያስፈልግም። በተመሣሣይ በኮሮና ቫይረስ ከፍተኛ ህዝብ ያለቀባት የአሜሪካ ኒዎርክ ግዛት/ከተማ ናት። እዚህም ቢሆን እስከ March 12/2020 ድረስ በኒውዮርክ ከተማ የሚገኘው Madison Square Garden እስከ 100 ሺህ የሚደርሱ ተመልካቾች በተገኙበት የስፖርት ጨዋታዎችን ሲመለከቱ ነበር።
በኢጣሊያንና አሜሪካ ኒውዮርክ የደረሰው እልቂት እያየንና እየሰማን እኛም በትላንቱ የፋሲካ ገበያ ላይ ኢትዮጵያ ውስጥ በትክክል ተደግሟል። ታዲያ… ትዕይንቱን ብቻ ሳይሆን እልቂትና መከራውን፣ በኮሮና የተያዙና የሞቱ ሰዎችን መቁጠሩን ልክ እንደ ሚላን እና ኒውዮርክ በአዲስ አበባም ይደገማል። “የሰው ልጅ “ሃ” ብሎ በሳር “ዋ” ብሎ ባሳር ይማራል” እንደሚባለው በቃል ሲነገረው ያልሰማ ህዝብ በመከራ ሊማር ወስኗል