በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን የምስራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት በሐረሪ ክልል ፖሊስ ላይ ስሞታ አቀረበ

DW : በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስትያን የምስራቅ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት በሐረሪ ክልል ፖሊስ ላይ ያቀረበው ስሞታ በቅርቡ በሀረር ከተማ ከጥምቀት በዓል ጋር በተያያዘ የተፈጠረውን ኹከትና ብጥብጥ ተከትሎ የክልሉ መንግሥት እና በተለይም የፀጥታ ኃይሉ ድርጊት አግባብ አይደለም ሲል የምሥራቅ ሀርጌ ሀገረ ስብከት ተቃወመ።

ሀገረ ስብከቱ ባወጣው መግለጫ የፀጥታ ኃይሉ ከበዓሉ ጋር በተያያዘ በተከሰተው ኹከትና ግርግር ሊጠየቁ ይገባቸው የነበሩ አካላት ላይ ሳይሆን በዓሉን ለማክበር በወጣው ሕዝብ ላይ መሣርያ ተኩሷል ፤ አስለቃሽ ጭስ ተጠቅሟል ፤ ንብረት እንዲወድም ዕድል ሰጥቷል ብሏል። የሀረሪ ክልል ፖሊስ ኮምሽን በበኩሉ ፖሊስ ምንም ዓይነት አስለቃሽ ጭስ እና ኃይል እንዳልተጠቀመ በመግለፅ፤ በየትኛውም አግባብ የሚቀርቡ ቅሬታዎች ካሉ በጋራ ተቀራርቦ ለማየት ዝግጁ መሆኑንን አመልክቷል።