የፌዴራል ሥርዓቱም ወደ ኣሃዳዊነት እየሄደ መሆኑን ተረድቼያለሁ – የኦሮሞ ፖለቲካ አቀንቃኝ ጀዋር መሀመድ

የኢህአዴግ አባል ድርጅቶችን ውህደትንም የፌደራል ስርዓቱን የሚሸረሽር ሲል ተችቷል።

DW : የኦሮሞ ፖለቲካ አቀንቃኝ ጀዋር መሀመድ በጀርመኗ ኑርንበርግ ከተማ ከደጋፊዎቹ ጋር በቀጣዩ የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ላይ ባለፈው ቅዳሜ ከመወያየቱ አስቀድሞ ዶቼቬለ በኑርንበርግ ቃለ መጠይቅ አድርጎለት ነበር።

የኦሮሞ ፖለቲካ አቀንቃኝ ጀዋር መሀመድ በጀርመኗ ኑርንበርግ ከተማ ከደጋፊዎቹ ጋር በቀጣዩ የኢትዮጵያ ፖለቲካዊ እንቅስቃሴ ላይ ባለፈው ቅዳሜ ከመወያየቱ አስቀድሞ ዶቼቬለ በኑርንበርግ ቃለ መጠይቅ አድርጎለት ነበር።ጀዋር በዚሁ ቃለ ምልልስ ላይ በግንቦት ምርጫ ይካሄዳል ተብሎ በሚጠበቅባት በኢትዮጵያ ከመንግስትም ሆነ ከተቀናቃኝ የፖለቲካ ኃይሎች በኩል እስካሁን በቂ የሚባል እንቅስቃሴ እየታየ አይደለም ሲል ወቀሷል።የፌዴራል ሥርዓቱም ወደ ኣሃዳዊነት እየሄደ መሆኑን ተረድቼያለሁ የሚለው ጃዋር ይህንኑ ለመታደግ ከወዲሁ አጀንዳ አድርጎ ስለመነሳቱም አብራርቷል።ጉዳዩ ዋነኛ የምርጫ መከራከሪያው እንደሚሆንም  ጀዋር ለዶይቸ ቬለ ገልጿል።

ጀዋር መሐመድ በሰሜን አሜሪካ እና በአውሮፓ የተለያዩ ሀገራት በሚያደርገው በዚሁ የቅስቀሳ ጉዞው በደጋፊዎቹ ከሚደረግለት አቀባበል ጎን ለጎን ተቃውሞም ገጥሞታል። በደረሰባቸው ስፍራዎች ተቃዋሚዎቹ በቅርቡ በኢትዮጵያ ከ80 ሰዎች በላይ ህይወትን ለቀጠፈው ደም አፋሳሹ ግጭት ተጠያቂው ጀዋር እንደሆነ ሲናገሩ ተሰምቷል። በኑርንበርግ ከተማም ተመሳሳይ የተቃውሞ ተሰምቷል። ጀዋር ስለዚሁ ጉዳይ ዶቼቬለ ላነሳለት ጥያቄ በሰጠው መልስ፣ «ተጠያቂ መሆን ያለበት ችግሩን የፈጠረው መንግስት ነው» ሲል ተናግሯል።

በተለያዩ መድረኮች የኢህአዴግን መዋሃድ ሲነቅፍ የሚሰማው ጀዋር በፓርቲው የውስጥ ጉዳይ ላይ ለምን ተቃውሞህን አሰማህ የሚል ጥያቄ ቀርቦለት ነበር። ኢህአዴግ የብልጽግና ፓርቲ ሆኖ የመዋሃዱን ነገር እንደ ጀዋር ሁሉ የቀድሞው የኢህአዴግ አባል ድርጅት የነበረው ህወሃትም በመቃወም ተለይቶ መውጣቱ ይታወቃል። ምንም እንኳ እስካሁን የመጨረሻ ውሳኔውን በጠቅላላ ጉባዔ ባያስወስንም። ጀዋር ህወሃትን በመደገፍ ይሆን የብልጽግና ፓርቲን የተቃወመው? ከዶቼቬለ የቀረበለት ሌላው ጥያቄ ነበር።

የኢትዮጵያ የመከላከያ ሚንስትር አቶ ለማ መገርሳ በጠቅላይ ሚንስትር አብይ አህመድ ተዘጋጅቶ የቀረበው እና ምናልባትም የሀገሪቱን ቀጣይ ፍኖተ ካርታ ያመለክታል የተባለለት የመደመር ፍልስፍናን እና የኢህአዴግን ውህደት እንደማያምኑበት ማሳወቃቸው በበርካቶች ዘንድ መነጋገሪያ ሆኖ ሰንብቷል።ስለዚሁ ጉዳይ ዶቼቬለ የጀዋርን አስተያየት ጠይቋል።

በኦሮሞ ህዝብ ስም የሚንቀሳቀሱ ሰባት የፖለቲካ ሀይሎች የመሰረቱት «ጋዲሰ ሆገንሰ ኦሮሞ» ወይም «የኦሮሞ አመራሮች በአንድ ጥላ ስር» በመባል የሚታወቀው ህብረት አቶ ለማ መገርሳን የህብረቱ አስተባባሪ አድርጎ መምረጡ ይታወሳል።

በኢትዮጵያ ሀገራዊ ምርጫ ላይ እንደሚሳተፍ ያሳወቀው ጀዋር አዲስ ፓርቲ በማቋቋም ወይስ ከነባሮቹ ተቀናቃኝ የኦሮሞ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር በመቀላቀል ነው በምርጫው የምትሳተፈው የሚል ጥያቄ ከዶይቸ ቬለ ቀርቦለት ነበር።

https://p.dw.com/p/3U6gl