ትግራይ በዜጎች ላይ በደል ፈፅሟል ያሉት ኃላፊ “ከሕግ አግባብ ውጪ በዋስ ተለቋል” ሲሉ ቁጣቸውን ገለጹ

VOA : በትግራይ ክልል ዓዲ ዳዕሮ ከተማ የሚገኙ ነዋሪዎች በዜጎች ላይ በደል ፈፅሟል ያሉት ኃላፊ “ከሕግ አግባብ ውጪ በዋስ ተለቋል” ሲሉ ዛሬ የተቃውሞ ሰልፍ ወጡ።

በሰሜን ምዕራብ ዞን የላይኛው አድያቦ ወረዳ ዓዲ ዳዕሮ ከተማ የሚገኙ ቁጥራቸው ወደ 15 ሺሕ የሚገመቱ ነዋሪዎች ተቃውሟቸውን የሚገልፁበት መፈክር ይዘው፤ ስሙን ለይተው በጠቀሱት አንድ የወረዳ አመራር ሳጅን አማካኝነት በዜጎች ላይ ደረሰ ያሉትን በደል በመዘርዘር ድምፃቸውን አሰምተዋል።

በሰልፉ ላይ የተሳተፉት ስለ ተቃውሞው ምክኒያት ሲናገሩ፤ በመንግሥት የሥራ ኃላፊነት ላይ የሚገኘው ግለሰብ ፤ በተለይ ቁጥራቸው ለጊዜ ያልተረጋገጠ ነገር ግን ከአስር በላይ የሆኑ ባለትዳር ሴቶችን በመድፈር በሴቶች ላይ ባደረሰው ተደጋጋሚ ጥቃት ምክኒያት ግምገማ ቀርቦበት ነበር።

በግምገማው ላይም ጉዳቱ ደርሶብናል ያሉ ሴቶች ፊት ለፊት እየተነሱ የምስክርነት ቃላቸውን ሰጥተው ነበር።

ከሴቶቹ በተጨማሪም በሐሰት በማስመስከር ወንዶች ያለ አግባብ እንዲታሠሩ አድርጓል በሚል ሰልፈኞቹ አቤቱታ አሰምተዋል። ከዚህ ግምገማ በኋላ ግለሰቡ እንዲታሰር ቢደረግም ብዙም ሳይቆይ ወዲያውኑ በዋስ እንዲፈታ መደረጉ ቁጣን ቀስቅሷል ብለዋል – የሰልፉ አስተባባሪዎች።

በሰልፉ ላይ ተሳታፊ ከነበሩት አንዱ ሌተናል ኮረኔል መኮንን አማረ ለአሜሪካ ድምፅ ስለ ሰልፉ ዓላማ ለአሜሪካ ድምፅ ሲያስረዱ፤ “ኅብረተሰቡ በተለይ በሴቶች ላይ የደረሰውን በደል ተቃውሞ ድምፃችን ይሰማ ሲል ነው አደባባይ የወጣው” ብለዋል።