የአይን እማኞች «በልዩ ሃይላትና በምዕመናን ውዝግብ 2 ሰዎች ተገደሉ 17 ሰዎች መቁሰሉ»
ትናንት ሌሊት ሰባት ሰዓት በአዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ ሃያ ሁለት በሚባለው መንደር ቤተ ክርስቲያን "እናፈርሳለን ፣ አታፈርሱም " በሚል በተፈጠረ የልዩ ሃይላትና የ ምዕመናን ውዝግብ 2 ሰዎች መገደላቸውና 17 ሰዎች መቁሰላቸውን በቦታው ሁኔታውን የተከታተሉ አንድ የአይን እማኝ ለዶቼ ቬለ ( DW ) አረጋገጡ።
የአይን እማኙ የሁኔታውን ጭብጥ ሲያስረዱ ከዚህ በፊት አይተናቸው የማናውቃቸው በርከት ያሉ ልዩ ሃይሎች ከሌሊቱ ሰባት ሰአት ላይ መጡ። ከዚህ በፊት ማለትም ከሶስት ቀን በፊት ቤተ ክርስትያኑን አፍርሱ ብለውን ነበር። እስከዚህ ድረስ ግን ይደርሳል ብለን አልገመትንም ነበር ብለዋል። ምሽት ላይ ጉባኤ ስለነበር ዘምረን ፣ መንፈሳዊ ስርአታችንን አከናውነን ስንመለስ ነበር ነገሩ የተከሰተው ብለዋል። ከመካከላችን ተለቅ ያለ ወጣት ሄዶ ለምን እንደመጡ ሲጠይቃቸው " ቤተ ክርስትያኑን በሰላማዊ ሁኔታ ለማፍረስ ነው የመጣነው" የሚል ምላሽ እንደመለሱለት ይህም ብዙ ወጣቶች ራሳቸውን መቆጣጠር እስኪሳናቸው እንዲቆጡ ማድረጉን፣ የቤተ ክርስቲያኑ አባቶችም የማንቂያ ደወል መደወል መጀመራቸውን ተናግረዋል። በዚሁ ቅጽበት ልዩ ሃይሎች ወደ ቤተ ክርስቲያኑ አስለቃሽ ጭስ መተኮስ መጀመራቸውንም አመልክተዋል። የሚተኮሰው አስለቃሽ ጭስ የጦር መሳሪያ ድምጽ ይመስል ስለነበር ብዙ ሰው መረበሹን፣ ወጣቶችም ድንጋይ መወርወር መጀመራቸውን አስታውሰዋል። የአይን እማኙ አክለውም " ሴት እና አረጋዊ እንደዚያ ሲረገጡ በህይወቴ አይቼ አላውቅም " ነው ያሉት። ይህንን ተከትሎ ፖሊሶች ድንጋይ መወርወር መጀመራቸውን ፣ የሰው ብዛት መጨመሩን ሲያውቁ መሳሪያ መተኮስ መጀመራቸውንና ከጎኑ የነበሩ ወጣቶች ሲወድቁ መመልከታቸውን እንዲሁም ሽጉጥም ወደላይ ወይም ወደታች ሳይሆን ፊትለፊት ይተኮስ እንደነበር ፣ ፖሊሶችም " እስቲ ና ውጣ " ይሉ እንደነበር ሰምቻለሁ ብለዋል። ከሞቱት መካከል አንደኛው ሚኪ የሚባል ጓደኛቸው እንደሆነና ረፋድ ላይ ለቅሶ ደርሰው እንደመጡም ለዶቼ ቬለ ተናግረዋል። የቀብር ስነ ስርአትም ሊከናወን ዝግጅት ላይ መሆኑን አክለው ገልጸዋል። እስካሁን ባለን መረጃ እግራቸው ፣ እጃቸው የተመታ እስከ 18 የሚደርሱ ሰዎች መቁሰላቸውንና ወደ ሆስፒታል መወሰዳቸውንም እናውቃለን ሲሉ ሁኔታውን ተናግረዋል። ጉዳዩን በተመለከተ ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት ወዳ አዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የህዝብ ግንኙነት ክፍል ተደጋጋሚ የስልክ ጥሪ ብናደርግም ለጊዜው ምላሽ ማግኘት አልቻልንም።
በተመሳሳይ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን መረጃ ለማግኘት ያደረግነው ያልተቋረጠ ጥረት ባለመሳካቱ ምላሻቸውን ልናካትት አልቻልንም።
- Category
- Ethiopian News