የመሬት ሊዝ ጨረታ ሊጀመር ነው ተባለ

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር አቋርጦት የነበረውን የመሬት ሊዝ ጨረታ በቅርቡ እጀምራለሁ አለ፡፡

ለ30ኛው ዙር የሊዝ ጨረታም መሬቶች እንደተዘጋጁ የመሬት ልማት ማኔጅመንት ጽ/ቤት ለሸገር ተናግሯል፡፡

ከዚህ በፊትም ጨረታው የሚስተናበርበት ሶፍትዌር ዳግም እየተፈተሸ ስለሆነ ይተላለፋሉ የተባሉት መሬቶች እንደተያዙ ሰምተናል፡፡

መሬቶቹ እንደ ከዚህ ቀደሙ ከነችግራቸው እንዳይተላለፉ ከፍተኛ ጥናት ተደርጎበታል ተብሏል፡፡

ወሬውን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመሬት ልማት ማኔጅመንት እና ማስተላለፍ ጽ/ቤት የመሬት ባንክ ቢሮ ሀላፊ አቶ ተስፋዬ ጥላሁን ለሸገር ነግረዋል፡፡

በ30ኛው ዙርም በጨረታ የሚተላለፉ መሬቶችን እንደከዚህ ቀደም እያጠሩ ማቆየት እንደማይቻል ሀላፊው ተናግረዋል፡፡

በጨረታ ያሸነፉት መሬት ምን ያህል ውድ እንደሆነ ተረድተው የሚገቡት ግዴታ እና ውል ተሰናድቶ ይጠብቃቸዋል ተብሏል፡፡

30ኛው ዙር የመሬት ሊዝ ጨረታም በቅርቡ እንደሚጀመር አቶ ተስፋዬ አስረድተውናል፡፡