የሰላም መሠረቶች — በቀለ ጉተማ (ፕሮፌሰር)

የሰላም መሠረቶች
***
በቀለ ጉተማ (ፕሮፌሰር)
****
የሰላምን ምንነት በአጭርና ቀላል መንገድ መግለጽ ከባድ ነው፡፡ ሰላም ሲኖር በቀላሉ የሚወሰድ፣ ሲደፈርስ ብቻ ዋጋው ምን ያህል ከባድና አስፈላጊ የሆነ በትውልዶች መፈራረቅ የዳበረ እሴት መሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡ ሰላም ከጥንት ፈላስፎች እስከቅርብ ጊዜ ሊቃውንት የተጠበቡበት ለሰው ልጆች በጣም አስፈላጊ የሆነ እሴት ነው፡፡ ፍልስፍናዊ መሠረቱን መፈለግ ጠቃሚነቱን ለማጉላት ካልሆነ በቀር ሰላምን ሁሉም ይረዳታል፤ያውቃታል ማለት ይቻላል፡፡ ፍልስፍናዊ መሠረቱ ላይ የሚተኮረው ፈላስፎች በጉዳዩ ላይ እንዳሰቡበት ለማሳየት፤ ጥልቅ የሆነ ፍልስፍናዊ መሠረት እንዳለው ለመገንዘብና ፍልስፍና መሠረታዊ የሆኑ የኑባሬ፣ የዕውቀት፣ የሞራል መሠረቶች እንደሚያስጨብጠን የዕውቀት መስክ ምን ያህል በሰላም ላይም እንደተጠበበ ለማሳየት ነው፡፡

የሰላምን ምንነት ለመረዳት ሰላም የግጭትና ጦርነት አለመኖር፣ በሰዎች መካከል የመቀራረብ፣ የመግባባትና ግጭቶችን ያለጥልና ጉልበት የመፍታትና የመምራት ሁኔታን ይመለከታል፡፡

ከዚህ ባሻገር ግን ዕውቅ ፈላስፎች ከፍልስፍና አንጻር የሰላምን ምንነትና ዋጋ ለማስረዳት ሞክረዋል፡፡ በቀላሉ ሰላምን የእሱ ተቃራኒ በሆነው ጦርነትና ቅራኔ መረዳት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ጠለቅ ብለን ከሰው ልጆች ሕይወትና የኑሮ ግብ አንጻር ሰላምን መረዳት ጠቃሚ ነው፡፡ ይህንን ማለት ስለ ሰው ልጆች ሕይወት ግብ ምንነት መመራመር ነው፡፡

የሕይወት ግብ በቀላሉ ፍላጎቶቻችንን በሥራ አሟልተን ከሰውና ተፈጥሮ ጋር ተግባብተን መኖር ነው፡፡ ይህ እንግዲህ በተለያዩ የታሪክ ሁኔታዎች ውስጥ የሚከናወን እንደመሆኑ መጠን ግቡ አንድ ቢሆንም በተወሳሰበ ማኅበረ ኢኮኖሚያዊ ሁኔታ ውስጥ እንደሚከናወን መረዳት ተገቢ ነው፡፡ በሕይወታችን ውስጥ ሠርተን፣ ፍላጎቶቻችንን አሟልተን ምሉዕና ደስታ የተሟላበት ኑሮ መኖር እንፈልጋለን፡፡ እንደ አንዳንድ ፈላስፎች አገላለጽ የሕይወት ግብ ራሱ ደስታን መሻት ነው፡፡ ደስታን ለመሻትና ለማግኘት ደግሞ ያለሰላም አይቻልም፡፡ ይህ የሕይወት ግቡ እራሱ ሰላም ነው ወደሚለው አስተሳሰብ ይወስደናል፡፡ ያለሰላም ደስታን መፈለግና ማግኘት ቀርቶ መኖርም ስለማይቻል የሕይወት ግቡ ራሱ ደስታ ነው፡፡ የፖለቲካ ግብ ሰላም ነው፡፡ ምክንያቱም ሰላምን ሁሉም ሰው ስለሚፈልገው፡፡ ሰላም ሁሉን ዐቀፍ/ሁለንተናዊ ተፈላጊነት አለው፡፡ ሁሉም በተግባር ይፈልገዋል/ይፈቅደዋል፡፡ ይህ ለሰላም የተለየ ዋጋ ይሰጠዋል፡፡

ስለሰላም አስፈላጊነት መርህ በምንናገርበት ጊዜ ሰላም በተግባር በዕውን የሚፈለግ በሥነ ምግባር አስገዳጅነት ላይ የተመሠረተ ነው በሚል ግንዛቤ ነው፡፡ የእንግሊዝኛው አባባል በትክክል የሚገልጸው ከሆነ፣ “peace is not only practically inevitable but is also a moral imperative” ማለት ነው፡፡

ሰላም የሰብአዊነት ከፍተኛ እሴት እንደመሆኑ መጠን ከሁሉም በላይ ነው፡፡ ለሰላም ሲባል ሁሉንም ነገር መተው ይቻላል የሚሉ ቢኖሩም ይህንን ግን በደፈናው ለመቀበል ያስቸግራል፡፡ ከጦርነት ጋር በማወዳደርም ኢፍትሐዊ የሆነ ሰላም ከፍትሐዊ ጦርነት ይመረጣል ይባላል፡፡ በመሆኑም ጥሩ ጦርነት የሌለውን ያክል መጥፎ የሆነ ሰላም የለም እንደማለት ነው፡፡ በዚህ ነጥብ ላይ ወደ መጨረሻ ላይ እመለስበታለሁ፡፡

ስለዚህ በሃይማኖትም ይሁን በፍልስፍና ሰላም ከፍተኛ ቦታ ያለው ሆኖ ሰላምን እንደጦርነትና ጉልበት ተቃራኒ እና የመሳሰለው መረዳት የተለመደ ነው፡፡ በእርግጥ በታወቁ ፈላስፎችና የሃይማኖት ሊቃውንት/አባቶች ዘንድ ስለ ሰላም ያለው ግንዛቤ በአብዛኛው የሚመሳሰልባቸው ነጥቦች ሲኖሩ በአጠቃላይ ሰላም የጦርነትና ቅራኔ አለመኖር ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ይህንን ሰላምን በተቃራኒው የመረዳት ሁኔታ በአዎንታዊ ስንረዳው ሰላም እንደ ስምምነት፤ መግባባት እና ፀጥታ ተደርጎ ሊወሰድ ይቻላል፡፡ ይህንን ሰፋ ባለ መልኩ ስንረዳ መጀመሪያ በግለሰብ ደረጃ ያለን ውስጣዊ/ አእምሮአዊ ሰላም፤ ከዚያም ከአካባቢ (ሰውና ተፈጥሮ) ጋር ያለ ሰላም፤ ብሎም የሕግና ሥርዓት መኖር፤ የፍትሕና መልካምነት ወይም በዘመናዊ አጠራሩ መልካም አስተዳደር፣ በመንግሥትና በሕዝብ፣ በሰውና ተፈጥሮ፣ እንዲሁም ሌሎች ይህንን በሚመለከት ጉዳይ ሊኖር የሚገባውን ሚዛናዊነት የሚያሳይ ሁኔታ ሰላምን/የሰላምን መኖር የሚያስረዳ ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡

እስካሁን እንደመግቢያ ለማንሳት የሞከርኩት ሰላም ምን ማለት እንደሆነ፣ ሰላም ደግሞ ከፍልስፍና አንጻር እንደሚታይ ባጭሩ ለመግለጽ ነው፡፡ በሁሉም ባህሎችና እምነቶች እንዲሁም ሕዝቦች ዘንድ ሰላም ከፍተኛ ዋጋ አለው፡፡ ሰላምን የማያስተምር እምነት የለም፡፡ ፈላስፎችም ሰላምን ከሞራላዊነት መርሆዎች ጋር በማገናኘት የሚረዱት ሲሆን ሰላም በምን መንገድ ነው የሚከበረው/የሚሰፍነው በሚለው ላይ ሊለያዩ ይችላሉ፡፡ በአብዛኛው የሚታወቀው ሰላምን ለማስከበር በተለይም በመንግሥት ደረጃ ለጦርነት ዝግጁ መሆን ነው የሚል ግንዛቤ አለ፡፡ ሁለቱ ተቃራኒዎች ናቸው፡፡ አንዱ ያለሌላው ትርጉም የለውም፡፡ ሰላም ለማስፈን ደግሞ መሣሪያው ጦርነት ነው የሚል ግንዛቤ መኖርና በአብዛኛውም ጦርነት ሰላምን የማስከበርያ መንገድ፣ ሰላምን የሚያደፈርስን የመከላከያ መንገድ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡

ነገር ግን እንደዚህ ዓይነቱ ግንዛቤ ዘላቂ ሰላምን ለማስፈን በቂ ስለማይመስለኝ ባህላዊና ኅብረተሰባዊ፣ እንዲሁም ፍልስፍናዊ መሠረቱ ላይ ማተኮሩ ተገቢ ነው፡፡
በዚህ ረገድ በገዳ ሥርዓት ውስጥ ያለው የሰላም ግንዛቤ ትኩረትን የሚሻ ነው፡፡ የገዳ የሰላም ጽንሰ ሐሳብ በገዳ ሥርዓት ውስጥ ባሉ እሴቶች ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ሰላምን በሰዎችና ሰዎች መካከል ካለው ግንኙነት ባሻገር ሁሉን በሚያቅፍ መልኩ መረዳት ይቻላል፡፡
ሰላም የሚወሰነው ግለሰቦች ወይም ኅብረተሰብ በምን ደረጃ የሞራል መርህን ተከትለው መኖር ይችላሉ በሚለው ነው፡፡ የሞራል መርህ በገዳ ሥርዓት ሰፉ (Safuu) ይባላል፡፡ ሰላም ነጋ (Nagaa) ይባላል፡፡ ግለሰብ/ኅብረተሰብ በምን ያክል ደረጃ ሰፉ ከሰው የሚፈልገውን አሟልቶ ከራሱ፤ ከጎረቤቱና ከተፈጥሮ ጋር ተስማምቶ መኖር ይችላል የሚለው ወሳኝ ጉዳይ ነው፡፡ ይህም ስምምነትን በሁሉም መስክ (harmony) ሥርዓት (order) ሚዛናዊነት (balance) እና ፍትህ (justice) የተመለከተ ነው፡፡ ሰዎች ከራሳቸው ጋርና ከከባቢያቸው ጋር ሰላም ኖሯቸው ለጋራ ዕድገትና አብሮ መኖር አስተዋጽዖ ካደረጉ ሰላም አለ ማለት ነው፡፡ ኅብረተሰብ ውስጣዊና ውጭያዊ ስምምነት (harmony) ካለው ሰላም አለ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ሰላም ከፖለቲካዊ፤ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ኑሮ ባሻገር ሰዎች ከሰዎች ሰዎች፤ ከተፈጥሮና ከከባቢ ጋር ያለውን ግንኙነት ስለሚመለከት ሰላም ሁሉን ዐቀፍ (holistic) ይዘት አለው፡፡
በገዳ ሥርዓት በኅብረተሰብ ዕለታዊ እንቅስቃሴና በየጊዜው በሚከበሩ በዓላት እንደሰላም ቀዳሚውን ስፍራ የሚይዝ የለም፡፡ ግለሰብ ጧት በሰላም ያሳደርከኝ በሰላም አውለኝ ከማለት አልፎ፤ ለከባቢው፣ ለእንስሳቱ፣ ለወንዙ ወዘተ. ሰላም እንዲያገኙ ይመኛል፤ይፀልያል፡፡ በበዓላት ጊዜ የሚደረጉ ፀሎቶች ላይ ሰላም ከቀዳሚ ርዕሶች የመጀመሪያው ነው፡፡ ይህ የሰላምን መሠረታዊነት ያሳያል፡፡

እንዲህ ዓይነት ግንዛቤ የሚመነጨው በኅብረተሰቡ ውስጥ ካለው የዓለም አተያይ (world-view/philosophy) ነው፡፡ ከገዳ ሥርዓት በስተጀርባ ያለው የዓለም አተያይ/ፍልስፍና በብዙ ሰዎች እንደተጻፈው ሥርዓት ባለው መንገድ ከላይ እስከታች ሕይወት ያለውና የሌለውን ጨምሮ እንደተሳሰሩ የሚያሳይ ነው፡፡ ይህ መተሳሰር ሥርዓት ከመሆኑም በላይ ከሥርዓቱ አካላት ውስጥ አንደኛው ከተናጋ ወይም ሰላም ካጣ አጠቃላዩም ሥርዓት ሰላም አይኖረውም፡፡ በዚህም የተነሳ ይመስላል በፀሎቶቹ ውስጥ ለሁሉም ሰላም እንዲሆን የሚፀለየው፡፡ የፀሎቱ ይዘት ቤቱም ደጁም ከብቱም ከባቢውም እና ሌላው ሌላው በሥርዓቱ የታቀፈው ሰላም እንዲኖረው ነው፡፡ በኦሮሞ ኮስሞሎጂ ያሉት ፍጥረታት ከላይ እስከታች በተለያዩ ድሮችና ማጎች የተሳሰሩ መሆናቸውን የሚያሳይና ከትስስሩ ውስጥ አንደኛው ሰላም ካጣ ሌሎቹም ሰላም የማይኖራቸው መሆኑን ነው፡፡ ይህ ሁሉን ዐቀፍ (holistic) የሆነ የሰላም ግንዛቤ ከፈጣሪ ጋር፣ ከራስ ጋር፣ ከጎረቤት ጋር፣ ከከባቢ ጋርና ሌሎችም ይህንን ኮስሞሎጂ ኮስሞሎጂ ከሚያሰኙት ሁሉም ጋር ያለው ትስስር ሰላም ካልሆነ ሥርዓቱ እንደሚናጋ ነው፡፡

ሰላምን ሁሉም ይፈልገዋል፤ ሰላም የግጭትና የጦርነት ተቃራኒ ነው፡፡ በዚህ ግንዛቤ መሠረት ሰላም የሞራል መርህ ዋነኛው ማሳያ ነው፡፡ የሰፉ መለኪያው የሰላም መኖር ነው፡፡ የሰላም መኖር ደግሞ የመኖር ዋስትና ነው፡፡ በሰላም ስንኖር ነው ትውለድ ተክተን፣ ሀብት አፍርተን እና ኅብረተሰብ አሳድገን ልናልፍ የምንችለው፡፡ በዚህም የተነሳ ሰላም በሰፉ ውስጥ ልዩ ቦታ አለው በማለት የገዳ ሥርዓትን ያጠኑ ምሁራን በተደጋጋሚ የሚያስተምሩት፡፡ በገዳ አስተምህሮት ውስጥ ካሉት እሴቶች አንዱና ዋነኛው የሰላም ጉዳይ ነው፡፡

በዚህም መሠረት የእርስ በርስ ግጭት ጨርሶ የተከለከለና የተኮነነ ነው፡፡ ከግጭት ይልቅ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው መተሳሰብ፣ ያለውን መካፈል (caring and sharing) ነው፡፡ የገዳና ቃሉ ተቋማት አንዱ ተግባራቸው ይህንኑ በኅብረተሰብ አባላት መካከል የሚኖረውን ውስጣዊ ሰላምና ትብብር መኮትኮት ነው፡፡ የሰው ልጅ ማድረግ ያለበት ሰላምን የሚያሰፍኑ ነገሮችን ብቻ እንደሆነ የገዳ አስተምህሮ ይነግረናል፡፡ ሰዎችንና አካባቢን ከሚጎዱ ነገሮች መታቀብ፤ በንግግሮቻችን ሌሎችን በማክበር በኅብረተሰብም ውስጥ ሆነ በተፈጥሮ ውስጥ ያላቸውን ቦታ/ሚና ባለመንፈግ ሰላምን ለማስፈን አስተዋጽዖ ማድረግ ይቻላል፡፡ በባህልና አኗኗር ከሚመስሉን ጋር ውስጣዊ ሰላም፤ ከማይመስሉን ጋር በይነ ባህላዊ ብቃት (intercultural competence) በተሞላበት ሁኔታ ግንኙነቶችን ማካሄድ፤ ይህም ሲባል የሌላውን ባህል፤ ፍላጎት ወዘተ መረዳት፤ ይህ በማይቻልበት ሁኔታ የመቻቻል ባህልን በማዳበር ሰላምን ማስፈን ተገቢና የሚቻል ነው፡፡ ስለሰላም በምናወራበት ጊዜ እራሳችንን መጠየቅ ያለበን ጉዳይ የመኖር ግቡና ዓላማው ምንድነው የሚለውን ነው፡፡ ሃይማኖታዊና ፍልስፍናዊ ግቦችን ለጊዜው አቆይተን መኖርን በተራ ግንዛቤ ስናየው አላማና ግቡ እላይ እንደተጠቀሰው ፍላጎትን አሟልቶ ትውልድን ተክቶ ቁም ነገር ለትውልድና ሀገር መሥራት ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ ሰላም ወሳኝ ነው፡፡ ሰላም በቅድሚያ በሕይወት ለመኖር ወሳኝ ነው፡፡ ከዚያ ባለፈ ግን ለሕይወት አስፈላጊ የሆኑ ነገሮችን ያለሰላም ለማሟላት አይቻልም፡፡ ይህም የሰላምን ወሳኝነት እንድናሰምርበት ያስገድዳል፡፡

እዚህ ላይ በገዳ ሥርዓት ላይ ያተኮርኩት ከሌሎች በተሻለ በእርሱ ላይ ግንዛቤ አለኝ ብዬ ስለማስብ እንጂ በሁሉም እምነቶቻችን፣ ባህሉቻችንና ፍልስፍናዎቻችን ሰላም ከፍተኛ ቦታ እንዳለው፣ የዳበሩ የቅራኔ አፈታት ዘዴዎችም እንዳሉ እገነዘባለሁ፡፡

ሰላም ያስፈልጋል ስንል ተዲያ ለሰላም የሚያስፈልጉ ነገሮችን ባለመርሳት መሆን አለበት፡፡ ብዙ ጊዜ የፖለቲካ ሰዎች ሰላምን ከሁኔታዎች ነጥለው ሲሰብኩ ይሰማል፡፡ በመሠረቱ ሰላምን የሚጠላ ጤነኛ ሰው ያለ አይመስለኝም፡፡ ስለዚህ ሰላም የሚጠፋው በሰዎች ሰላም አለመፈለግ ሳይሆን በአካባቢያችን ባሉ አኗኗራችንን በቀጥታም ይሁን በተዘዋዋሪ የሚነኩ፤ ሰላምን የሚጻረሩ ነገሮች ሲኖሩ ነው፡፡ ፖለቲካና ሌሎች የሰው ልጆች ተግባራት ለሰላም መኖር ወይም መጥፋት ትልቁን ድርሻ ይወስዳሉ፡፡ በሕዝብ ዘንድ ተቀባይነት ያለው የፖለቲካ ሥርዓትና አስተዳደር ከሌለ በተለይም ፍትሕ ከተጓደለ ሰላም ሊኖር አይችልም፡፡ ፍትሕ በሌለበት ሁኔታ ሰላምን የሚሰብክ ፖለቲከኛም ሆነ ፈላስፋ፣ የሃይማኖት አባትም ይሁን ባህላዊ መሪ እራሱን መጠየቅ ያለበት ጉዳይ በእርግጥ አሁን ያለንበት ሁኔታ ሰላምን ሊያሰፍን የሚችል ነወይ ብሎ መሆን አለበት፡፡ ፍትሕን ለሕዝብ ነፍጎ ሰላም ማስፈን አይቻልም፡፡

እውነተኛ ሰላም ደግሞ በወታደር፣ በፖሊስ ባጠቃላይ በጠመንጃ ኀይል ሊሰፍን አይችልም፡፡ ጠመንጃና ጉልበት በጊዜያዊነት ፍትሕ የተነፈገ ሕዝብን ዝም ሊያሰኝ ይችላል፡፡ ይህ ግን ለተወሰነ ጊዜ ነው፡፡ ለዚህ የሩቁም የቅርብ ጊዜ ታሪካችንም ቋሚ ምስክር ነው፡፡ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ስለሰላም አስፈላጊነት ሰምተናል፡፡ የሰላም መጥፋት ለልማት እንቅፋት እንደሆነም ከሃይማኖት አባቶች ሳይቀር በሰፊው ተሰብኮልናል፡፡ ነገር ግን ዋናው ጥያቄ መሆን ያለበት ሰላሙ የጠፋው ሰው ሰላም ጠልቶ ነው ወይስ ፍትህ ፈልጎ ማለት ነው፡፡

በዚህ ረገድ እላይ ያነሳሁትን አንድ ሐሳብ መልሼ ማንሳት እፈልጋለሁ፡፡ ጥሩ ጦርነት ወይም መጥፎ ሰላም የለም የሚል ሐሳብ አንስቼ ነበር፡፡እንዲሁም ከፍትሐዊ ጦርነት ኢፍትሐዊ ሰላም ይሻላል የሚል ሐሳብም አንስቼ ነበር፡፡ እዚህ ላይ መጤን ያለበት ሁለቱ ተጻራሪ እንጂ ተደጋጋፊ እንዳልሆኑ ነው፡፡ በአስገዳጅ ሁኔታ ውስጥም የተባለው ምርጫ (መጥፎ ሰላም ከጥሩ ጦርነት) ሊደረግ ይችል ይሆናል፡፡ ይህ ግን በጣም አስገዳጅ በሆነ አጭር ጊዜ ውስጥ ካልሆነ በምንም ሁኔታ የሚመረጥ ካለመሆኑም በላይ ሰላም ያለ ፍትሕ ምንም መሠረት እንደሌለው ነው፡፡ በጉልበትና በጠመንጃ የሚጠበቅ ሰላም ጉልበቱ የደከመ ዕለት/ጠመንጃው የዶለዶመ ዕለት ፍርክርኩ ይወጣል፡፡ ሰላምን ለማስፈን ቢያንስ በጣም በትንሹ (minimum) በሚባል ደረጃ ለሰው በሕይወት መኖር ዋስትና መስጠት ይጠይቃል፡፡ ያ ሳይሟላ ሰላምን መመኘት አይቻልም፡፡ ቢመኙም እንኳን ባዶ ምኞት ይሆናል፡፡

ስለሰላም አስፈላጊነት በምናወራበት ጊዜ ያለፉትን የኢትዮጵያ ሐምሳ ዓመታትና ከዚያ በላይ ጉዞ ማጤን ተገቢ ነው፡፡ ጦርነት የኢትዮጵያ የረጅም ጊዜ ታሪክ አካል ነው፡፡ በተለይም ከ1953 ዓ. ም. የጄኔራል መንግቱ ንዋይ የመንግሥት ግልበጣ ሙከራ አንስቶ አንዴ ቦግ አንዴ እልም በሚል የጦርነት ሁኔታ ውስጥ ስለነበርን የተሟላ ሰላም ኖሮን ያውቃል ማለት አይቻልም፡፡ ይህ ደግሞ አዲስ ፍትሐዊ የሆነ ሥርዓት/ኅብረተሰብ የማዋለጃው መንገድ ጉልበት ብቻ ነው የሚለው አስተሳሰብ በውስጣችን ስለሰረፀ ሳይሆን አይቀርም፡፡ የሆነ ሆኖ እነኚህ ፍትሕን በጉልበት የማምጣት ሙከራዎች ምን ያህል መከራ እንዳመጡብን የምናውቀው እኛ ነን፡፡ በእርግጥ ከዚህ የረጅም ጊዜ ሙከራ በኋላ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ይቅርታን፣ ፍቅርንና ሰላምን እየሰበኩ በዚያው መንገድ ለውጥ ማምጣት እንደሚቻል ለማሳየት እየሞከሩ ነው፡፡ ይህንን አስተሳሰብ ከነበርንበት ሁኔታ አንጻር በቶሎ ለመቀበል አስቸጋሪ እንደሆነ መገመት አያዳግትም፡፡ የሆነ ሆኖ ለግማሽ ምዕተ ዓመት ሞክረነው ያገኘነውን ነገር ስለምናውቅ ላልሞከርነው ሰላም/ሰላማዊ መንገድ ዕድል ብንሰጥ የምናጣው ነገር ምንድው? በሰላምና ከሰላም የምናጣው ነገር የለም፡፡ ምንም ቢሆን በሰላም የምናጣው በጦርነት ካጣናው ጋር የሚወዳደር አይደለም፡፡ ይህ ብቻም ሳይሆን በዚያው በጉልበት መንገድ ብንቀጥል አገራችንና ሕዝባችን ሊሸከሙት ይችላሉ ወይ የሚለው ጥያቄ ወሳኝ ነው፡፡

ያለፉት ዓመታት ኅብረተሰባችንን ያስተሳሰሩት ክሮች እየላሉና እየተበጣጠሱ የመጡበትና ተስፋ መቁረጥ የተንሰራፉበት ስለሆነ ከበድ ያሉ መንገራገጮችን (shocks) ልንቋቋም የማንችልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል፡፡ በመሆኑም በጉልበቱ መንገድ ብንቀጥል ተመልሰን ልናንሰራራ በማንችልበት ደረጃ ልንጠቃ እንችላለን፡፡ ለሰላም ካሉት ሃይማኖታዊና ፍልስፍናዊ ምክንያቶችም በሚያመዝን መልኩ ያለንበት ተጨባጭ ሁኔታም ‹ፕራግማቲክ› ሆነን ሰላምንና የሳላምን መንገድ መውሰድ አማራጭ የሌለው መሆኑን ያሳየናል፡፡

አሁን በኢትዮጵያ ለመጣው ለውጥ ወጣቶቻችን የአንበሳውን ድርሻ እንደሚወስዱ ግልጽ ነው፡፡ ወጣቶቻችን ፍርሃትን በማሸነፍ በድፍረት ጥይትን፣ እሥራትን፣ ዱላን ሳይፈሩ ባደረጉት በአብዛኛው ሰላማዊ የሆነ እነርሱ ግን ከፍተኛ መስዋዕትነት የከፈሉበት ሁኔታ ትርጉም ያለው ለውጥ ልናመጣ የምንችልበት የፖለቲካ ድባብ ለመፍጠር አስችለውናል፡፡ አሁን ለውጡ ሥርዓት ይዞ የፖለቲካ ምኅዳሩን አስፍቶ እንዲጓዝ፣ እንደበፊቱ ሁሉም በሰከነ ሁኔታ እየተሳተፈ እንደሚገኝ እሙን ነው፡፡ ይህ ማለት ግን በወጣቶችም ይሁን በሌሎች አካላት ዘንድ ያለው ሁኔታ አመርቂ ነው ማለት አይቻልም፡፡ በተለይም ደግሞ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ውስጥ አልፎ አልፎ የሚታየውና በብሔር ተከፋፍሎ ግጭት ውስጥ የመግባት ነገር አሳሰቢ ብቻ ሳይሆን ከወጣቱ የሚጠበቅ አይደለም፡፡ በተለይም ደግሞ በከፍተኛ ደረጃ የተማሩ ወጣቶች ተግባራቸው መሆን ያለበት መመራመር፣ ማጥናት፣ የኅብረተሰብ ችግሮችን መፍታት፣ ቅራኔዎችን በውይይት መፍታት እንጂ ወደ ጠብና ዱላ መሄድ ትምህርታቸውን ጥያቄ ውስጥ ይከታል፡፡

በቋንቋ፣ በእምነት፣ በባህል፣ በታሪክና በመሳሰለው እንለያይ እንጂ በመሠረቱ ሁላችንም ኢምንት ልዩነት ብቻ ያለን፡፡ ሳይንስ እንደሚነግረን 99.90 በመቶ አንድ የሆንን የሰው ልጆች ነን፡፡ በብሔረሰቦች መካከል በተለያዩ ምክንያቶች እውነተኛ የሆኑ ያልሆኑም ቅራኔዎች ነበሩ፤ አሉም፡፡ በተለይ በታሪክ አባቶቻችንና አያቶቻችን መካከል ለነበረው ቅራኔ ዛሬ በጉልበት መፍትሔ እንሰጣለን ብለን ማሰብ አንችልም፡፡ ቅራኔዎችን የመፍቻውና የተነፈግነውን ፍትሕ የማስገኛው መንገድ፣ በተለይም አሁን በሰለማዊ የፖለቲካ ትግል መሆን አለበት፡፡ ዛሬ ተማሪዎች የሆኑና ከተለያዩ ብሔሮች የተገኙ ወጣቶች እንዴት እንደጠላት ሊተያዩ እንደሚችሉ መረዳት አዳጋች ነው፡፡ ከትግራይ፣ ከአማራ፣ ከኦሮሞ፣ ከሲዳማ፣ ከወላይታ፣ ከጉራጌ፣ ወዘተ. አርሶ አደሮች ወይም ሌሎች የኅብረተሰብ ክፍሎች የሚወለዱ ወጣት ተማሪዎችን ጠላት የሚያደርጋቸው ምን ምክንያት አለ? ለሁላችንም መጨቆን ምክንየት የሆኑ ገዢዎችና ሥርዓቶች ነበሩ፤ አሉ፡፡ ትግሉ መሆን ያለበት እንዴት ተባብረን ሥርዓት ቀይረን ሁላችንንም በዕኩልነት የሚያስተናግድ ሥርዓት መመሥረት እንጂ እንደ እኛው በችግር ውስጥ አልፎ በስንት መከራ ከኛ ጋር የሚማርን ተማሪ እንደጠላት ቆጥሮ ማጥቃት በማንም ቢደረግ በምንም መለኪያ ተቀባይነት የለውም፡፡

በፍልስፍናና በሃይማኖቶች ውስጥ ስላለ የሰላም ግንዛቤ በተለይም በገዳ ሥርዓት ውስጥ ስላለ ባህላዊ የሰላም ግንዛቤ በጭሩ አንስቻለሁ፡፡ ይህንን በምልበት ገዜ ግን በአገራችንና በዓለም ደረጃ ምን ያህል ለውጦች እንደተካሄዱ ባለመረዳት አይደለም፡፡ በእርግጥ በትምህርትና በሌሎች መንገዶች ያደረግናቸው ኢኮኖሚያዊ፣ ማኅበራዊና ባህላዊ ግንኙነቶች በባህሎቻችን ውስጥ ያሉትን ብዙ እሴቶች በማወቅም ይሁን ባለማወቅ እንድንረሳቸው ብቻ ሳይሆን እንድንንቃቸውም አድረገውናል፡፡ እንግዲህ እንደዚህ ፈታኝ ሁኔታዎች ውስጥ ስንሆን ግን የተወሰነ የራሳችንን እሴቶች፣ ባህሎችና የመሳሰሉትን ነገሮች ለመፈለግ እንገደዳለን፡፡ ወደመጣንበት እንድናተኩር፣ እራሳችንን እንድንፈልግ ካብራል እንደለው ወደመነሻችን እንድንመለስ የራስን ኅሊና ወደመፈተሽ (soul searching) እንሄዳለን፡፡ ይህ ደግሞ አስፈላጊ ነው፡፡ ስለዚህ ሰላምን በመፈለጉ ጥረት የአሁኖቹን ችግሮቻችንን ብቻ ሳይሆን ያለፈውን ታሪካችንን፣ የነበሩ ባህሎቻችንና እሴቶቻችንን ለመጠቀም መሞከር አስፈላጊ ይመስኛል፡፡

ይህንን ጽሑፍ ከማጠቃለሌ በፊት ጥቂት ሐሳቦችን ከማህትማ ጋንዲና ከማርቲን ሉተር ኪንግ ለማንሳት እፈልጋለሁ፡፡ የሕንድ የነፃነት አባት የሆነው ጋንዲ ፀረ-ቅኝ አገዛዝ ትግሉን በድል የተወጣው በሰላማዊ መንገድ ነው፡፡ ሰላማዊ ትግል ዋጋ እንደሚያስከፍል የታወቀ ቢሆንም ምናልባት ጦርነት ከሚያስከፍለው ሊያንስ ይችላል፡፡ ዋናው ነገር ግን በሰላማዊ መንገድ የተገኘ ድል ዘላቂነት ይኖረዋል፡፡ ይህ ብቻም ሳይሆን በሰላም ትግል የማካሄድ እንቅስቃሴ የሚመሠረትበት መርህ ከሰው ልጅ የኑሮ ግብና ዓላማ፤ ከሕይወት ምንነት፣ ከሰላምና ግጭት/ጦርነት ተቃራነነት አንጻር ሲታይ የሰላም መንገድ ሚዛን ስለሚደፋ ነው፡፡ በርግጥ ጋንዲ “ጉልበት የእንስሳት እንደሆነ ሁሉ ሰላም የሰው ልጆች መንገድ ነው፡፡ ጉልበትን ብቻ የሚረዳ እንስሳ ብቻ ነው፡፡ ምክንያቱም በነሱ ዘንድ መንፈስ ንቁ አይደለም፡፡ የሰው ክብር ከፍ ላለ ሕግ (የመንፈስ ጥንካሬ) መገዛትን ይጠይቃል፡፡ በጉልበት የተገኘ ድል ከሽንፈት እኩል ነው፡፡ ምክንያቱም ጊዜያዊ ስለሆነ፡፡ ደካማ ይቅር ማለት አይችልም፤ ይቅርታ የትልቅነት/የጥንካሬ ምልክት ነው፤” ይላል፡፡

ጋንዲን በሚያስታውሰን መልክ ማርቲን ሉተር ኪነግም “ጨለማ ጨለማን አያስወግድም፤ ጨለማን የሚያስወግድ ብርሃን ብቻ ነው፡፡ ጥላቻ ጥላቻን አያጠፋም፤ ፍቅር ጥላቻን ያጠፋል፤” በማለት የሰላምን ምንነትና ወሳኝነት ገልጿል፡፡
ሁለቱም በሚጠሉት ጉልበት (violence) በመሣሪያ ቢገደሉም በሰላማዊ መንገድ ለኅብረተሰቦቻቸው ከፍተኛ አስተዋጽዖ አድረገዋል፡፡ ከተግባራቸውም ሆነ፣ ካለንበት ሁኔታ ካለፈው ታሪካችንም ሆነ ባህሎቻቸን ስለሰላም የምናገኘው ግንዛቤ ሰፊ ነው፡፡ ለዐሥርተ ዓመታት ከነበርንበት የሰላም መጥፋት ሁኔታ ወጥተን ወደፊት ልንሄድ የምንቸለው ሰላም ሲኖር ነው፡፡ ፍትሕ የሌለበትን ሰላም የማንቀበልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል፡፡ አሁን ትልቁ የቤት ሥራችን መሆን ያለበት ሰላማዊ በሆነ መንገድ ፍትሕን በኅብረተሰባችን ውስጥ የምናሰፍንበትን መንገድ መሻት ነው፡፡