በአመፅና በትጥቅ ጥቃት ሳቢያ በሞሮኮ ኩባንያዎች ላይ ለሚደርስ ጉዳት የኢትዮጵያ መንግሥት ካሳ ለመስጠት ግዴታ ሊገባ ነው

በኢትዮጵያ መዋዕለ ንዋያቸውን በሚያፈሱ የሞሮኮ ኩባንያዎች ላይ ድንገተኛ በሆነ ሕዝባዊ አመፅ፣ የትጥቅ ጥቃት ወይም ተመሳሳይነት ባላቸው ክስተቶች ምክንያት ጉዳት ቢደርስ የጉዳት ካሳና መልሶ ማቋቋሚያ ክፍያን የሚያስገድድ ስምምነት መንግሥት ሊፈጽም ነው።

በኢትዮጵያና በሞሮኮ መንግሥት መካከል ኢንቨስትመንትን ለማበረታታትና ጥበቃ ለማድረግ የተፈረመውን ይህንን ስምምነት ለማፅደቅ ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ከሳምንት በፊት የተላከ ሲሆን፣ የምክር ቤቱ የውጭ ግንኙነትና የሰላም ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ስምምነቱን አስመልክቶ በአሁኑ ወቅት ዝርዝር ምርመራ በማድረግ ላይ ይገኛል። በሕዝባዊ አመፅ፣ በትጥቅ ውጊያ ወይም በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ምክንያት በሞሮኮ ኢንቨስትመንት ላይ ለሚደርስ የጉዳት ካሳና መልሶ ማቋቋሚያ የመስጠት ግዴታን በመንግሥት ላይ የሚጥለው ይህ ስምምነት፣ በተጨማሪም የመንግሥት ኃይሎች ወይም ባለሥልጣናት በሰጡት ትዕዛዝ ወይም በፈጸሙት ድርጊት ምክንያት፣ እንዲሁም ሁኔታዎች ሳያስገድዱ በመንግሥት ኃይሎች ወይም ባለሥልጣናት በኢንቨስትመንት ላይ ውድመት ወይም ጉዳት የደረሰ እንደሆነ ተመጣጣኝና ፍትሐዊ ካሳ የመክፈል ግዴታን ይጥላል።

በዚህ መንገድ ለሚደርሱ ጉዳቶች የሚሰጠው ካሳ ያላግባብ መዘግየት እንደማይኖርበት፣ የካሳ ክፍያ የተሰጠው ኩባንያም ክፍያውን በነፃነት አግባብነት ባለው የውጭ ምንዛሪ በመቀየር ከአገር የማስወጣት መብት እንደሚኖረው የስምምነቱ ይዘት ያስረዳል። ነገር ግን የካሳ ክፍያን ወይም በማንኛውም ወቅት ከኢንቨስትመንቱ የተገኘ ትርፍን በውጭ ምንዛሪ ቀይሮ የማስወጣት መብትን ስምምነቱ ቢፈቅድም፣ ሒደቱ በልዩ ሁኔታ በአገር የማክሮ ኢኮኖሚ ሥርዓት በተለይም በገንዘብ ምንዛሪ ፖሊሲ ላይ ከፍተኛ ችግር የሚያስከትል ከሆነ ከአድልኦ በነፃ መንገድ የገንዘብ ዝውውሩ ላልተወሰነ ጊዜ ሊታገድ እንደሚችል፣ ሆኖም ዕገዳው ሁኔታው ከሚወሰደው ምክንያታዊ ጊዜ በላይ መቀጠል እንደማይችል በስምምነቱ ተገልጿል።

የኢትዮጵያ መንግሥት ተመሳሳይ ይዘት የተካተቱባቸው የኢንቨስትመንት ማበረታቻና የጥበቃ ስምምነቶችን ከተወሰኑ አገሮች ጋር የፈጸመ ቢሆንም፣ በርካቶቹ መንግሥት የገባባቸው የሁለትዮሽ ስምምነቶች የተጠቀሱትን ግዴታዎች አይጥሉም።

ለአብነት ያህል በኢትዮጵያ ከፍተኛ መዋዕለ ንዋያቸውን በማፍሰስ ሰፊ እንቅስቃሴ ውስጥ ለሚገኙት የህንድ፣ የቱርክና የቻይና ኩባንያዎች የኢንቨስትመንት ጥበቃ ዋስትናና ማበረታቻ ለማድረግ ስምምነት የፈጸመ ቢሆንም፣ ስምምነቱ የተጠቀሱትን ግዴታዎች የሚጥል አይደለም። እንዲህ ዓይነት ስምምነቶች መንግሥትን በመወከል የሚፈራረመው የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር መሆኑን የገለጹት ሪፖርተር ያነጋገራቸው አንድ ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣን፣ ከፍተኛ ማበረታቻና ግዴታን በመንግሥት ላይ የሚጥሉ ስምምነቶች ውስጥ የሚገባው በሁለትዮሽ ደረጃ በሚደረግ ውይይት ነው፡፡ ኢንቨስትመንቱ የተለየ ጥቅም ወደ ኢትዮጵያ ይዞ እንደሚመጣ፣ ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ፋይዳ እንደሚኖረው ሲታመንበት ብቻ መሆኑን ተናግረዋል።

የሞሮኮ ንጉሥ መሐመድ ስድስተኛ ከአንድ ዓመት በፊት ኢትዮጵያን ሲጎበኙ  አጠቃላይ ወጪው ሁለት ቢሊዮን ዶላር የሚሆን ለእርሻ ግብዓት የሚሆን የማዳበሪያ ፋብሪካ ለመገንባት ስምምነት መፈጸማቸው፣ መንግሥትም ለግንባታው የሚሆን በድሬዳዋ ከተማ መሬት ማቅረቡ ይታወሳል። የፓርላማው ቋሚ ኮሚቴ በቀጣዮቹ ጥቂት ሳምንታት ውስጥ በስምምነቱ ላይ የውሳኔ ሐሳቡን በማቅረብ ስምምነቱ እንደሚፀድቅ ይጠበቃል።