የደህንነት መሥሪያ ቤት የኅይል አሰላለፍ እና “የወያኔ ኅይል”

የደህንነት መሥሪያ ቤት የኅይል አሰላለፍ እና “የወያኔ ኅይል”

(በረራ ጋዜጣ_ ታህሳስ 4/2011 ዓም)

የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት 7 መምሪያዎች አሉት። እነሱም፣ የውስጥ ደህንነት ጥበቃ ዋና መምሪያ፣ የውጭ ደህንነት ጥበቃ ዋና መምሪያ፣ የቴክኒክ ደህንነት ጥበቃ ዋና መምሪያ፣ የጥበቃ ዋና መምሪያ፣ የኢሚግሬሽንና የዜግነት ጉዳይ ዋና መምሪያ፣ የስደተኞችና ስደት ተመላሾች ዋና መምሪያ እና የክንፈ የብሔራዊ ደህንነት ማሰልጠኛ ተቋም ናቸው።

በደህንነት መሥሪያ ቤቱ ሁለት ኅይሎች አሉ። አንደኛው “የወያኔ ኅይል” የሚባለውና መሥሪያ ቤቱን የተቆጣጠረው ሲሆን ሁለተኛውና በጣም ጥቂት የሆነው ኅይል “የኢትዮጵያ ኅይል” ተብሎ የሚጠራው ነው።
የወያኔ ኅይል የተሰኘው አካል የደህንነት መሥሪያ ቤቱን ብቻ ሳይሆን ሀገሪቱን ተቆጣጥሮ ያሻውን ሲያደርግ የኖረ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ለተፈፀሙት የሰብአዊ መብት ጥሰቶች፣ የእርስ በእርስ ግጭቶች፣ ማፈናቀሎች፣ የዘረፋና የሌብነት ተግባር በቀዳሚነት የተሳተፈ ነው። የወያኔ ኅይል የሚባለው የመጀመርያ ዓላማው ትህነግ/ህወሓትን ስልጣን ላይ ማቆየት፣ የራሱን ብልፅግና እና ሀብት ማካበት ሲሆን ለዚህም ከትግራይ ልጆች ባሻገር ሌሎችንም በጥቅም ገዝቶ ወደ ጎራው ያስገባ ኃይል ነው።
በሌላ በኩል፣ “የኢትዮጵያ ኃይል” የሚባል በቁጥር ጥቂት ኅይል ያለ ሲሆን፣ የሁለቱ ክፍፍል ከ2008 እና 2009 ዓ.ም. በኋላ እየጎላ መጥቷል። የኢትዮጵያ ኅይል ተብሎ የሚጠራው ደህንነት መሥሪያ ቤቱ ለሀገርና ለሕዝብ መሥራት አለበት የሚል አቋም የሚያንፀባርቅ ሲሆን ከዘረፋ፣ ከሽብር ወንጀልና ሌሎችኝ ጉዳዮች ጋር በተፈጠረ አለመግባባት በ”ወያኔው ኅይል” የተባረሩ፣ የተገደሉ፣ የተሰወሩ የኢትዮጵያ ኅይል አባላት ይገኙበታል።

እነ ጌታቸው አሰፋ፣ በእነ አማኑኤል ኪሮስ፣ ያሬድ ዘሪሁን፣ መድህኔ ታደሰ፣ አደራጀው፣ ዶ/ር ሀሽም፣ ኢሳያስ ወልደጊዮርጊስ፣ ኅይለማርያም ገብሩ፣ ቴዎድሮስ ኅይሌ፣ በእነ አፅብሓ፣ በእነ ፍቃዱ ዓለማየሁ (ወዲ መርሳ)፣ ወዲ ፍሬው፣ ተወልደ፣ ተስፋየ ገ/ጊዮርጊስ፣ ገ/ዮሐንስ ተክሉ፣ በእነ ተመስገን ተክሉ፣ በእነ ጨርቆስ ተጫነ፣ በእነ ሀዱሽ ወዘተ. የሚመራው የወያኔ ኅይል ጥያቄ የሚያነሱ ደህንነቶችን እየለዩ በመምታት ላይ እና በሴራ ከተቋሙ ሲያሰወግድ ኖሯል።

የወያኔ ኅይል በሚባለው 90 በመቶ ማለትም ከሀገር ውስጥ ደህንነት፣ ጥበቃ ዋና መምሪያ የሚገኙ 400 ደህንነቶች ውስጥ 360 ያህሉ የወያኔ ኅይል፣ 49 የሚሆኑት ብቻ የኢትዮጵያ ኅይል ናቸው። በተቋሙ ካሉት 4000 በላይ ይህ ተመሳሳይ ነው። የወያኔው ኅይል በብሔራዊ ደህንነት መሥሪያ ቤቱ የበላይነት የያዘ ነው። ከሕግና ሕዝብን ከከሀገር ውስጥ ስጋት ከመጠበቅ ይልቅ የህወሓት የበላይነት ለማስጠበቅ ሲሠራ የቆየ ጠባብ ኅይል ነው። በሀገር ሀብት በውጭም ሆነ ሀገር ውስጥ የሚሰበስበውን መረጃ የሚያውለው ለህወሓት ግብአት ነው። የደህንነት መሥሪያ ቤቱ ‘ሪፎርም’ እያደረገም በነበረባቸው ባለፉት ወራት የወያኔ ኃይል ሕቡዕ ለመሆን እየሞከረ የነበር ሲሆን ዋና ዋናዎቹ በቅርቡ ተይዘዋል።

የወያኔውን ኅይል ሰንሰለት፤

1) አቶ ጌታቸው አሰፋ:- ከሥልጣን ከተነሳ በኋላ በዋነኝነት ሕዝብን ከሕዝብ ለማጋጨት ሲሠራ እንደነበር ይነገራል። ጌታቸው “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል፤” የሚለውን የህወሓትን ፖለቲካ በደህንነት ተቋሙ በኩል የሚመራ ሰው ነው።

የደህንነት መሥሪያ ቤቱ ውስጥ የማፍያ ፖለቲካውን ቁማር እየቀመረ በተላላኪዎቹ የሚያስፈፅም ሰው ነው። እሱም ሆነ በእሱ ስር ያሉት የወያኔ ኅይል አባላት ኢትዮጵያ ውስጥ ያለ ግጭትና ደም መፋሰስ ዋስት እንደሌላቸው የሚያምኑ ናቸው። በአማራና ቅማንት፣ በሲዳማ እና ወላይታ፣ በኦሮሞና ደቡብ (ጉጅ አካባቢ) የሚታዩት ግጭቶች ከእነዚህ ሥራዎች ያለፉ አይደሉም።

2) አቴ ኢሳያስ ወ/ጊዮርጊስ፡- የአቶ ጌታቸው አሰፋ ምክትል የነበረ፣ አሁን በውልና ማስረጃ ዳይሬክተር የሆነ ሰው ሲሆን፣ በወያኔኅይል አንዱና ወሳኝ አባል ነው።

3)አቶ ዘሬድ ዘሪሁን:- ምክትል የነበረ፣ በሙስና ምክንያት “ወዲ ሙስና” የሚባልና የፌደራል ፖሊስ ኮምሽን ኮምሽነር ተደርጎ እንደገና ደ ሁለት ወር ሳይሞላው የተነሳ፤

4) አቶ አደራው:- ቀደም ሲል የውጭ መረጃ ዳይሬክተር የነበረ፣ በቅርብ ምክትል ዳይሬክተር ጀኔራል የሆነ፤

5) ዶክተር ሀሽም፣ ምክትል ዳይሬክተር ጀኔራል የነበረ፤

6) አቶ ሙላቱ መኮንን (የብሔራዊ መረጃና ደህንነት ልዩ ጽ/ቤት ኅላፊ)፤

7) አቶ ማሾ ፣ ግዑሽ፣ እና አበበ ግደይ በተቋሙ የጌታቸው አሰፋ ቁልፍ ሰዎች የነበሩ፤

8/ አቶ ደሳለኝ ዑርጌሳ ለረዥም አመታት የብሔራዊ ደህንነትና መረጃ የአስተዳደርና ፋይናንስ ዳይሬክተር የነበረና ከሁለት ዓመታት በፊት የፌደራል ማረሚያ ቤቶች ኮምሽን ኮምሽነር፤

9) አቶ ተካና መዝሙር:- ሁለቱም የፌደራል ጠቅላይ ዐቃቤ ሕግ ረዳት አቃቤ ሕግ ዳይሬክተሮች ናቸው። አቶ ተካ የክርክር ጉዳዮች ዳይሬክተር ለረዥም ዓመታት በብሔራዊ ደህንነትና መረጃ አገልግሎት በኮተቤ 02 ክንፈ ማሰልጠኛ ማዕከል ምክትል ዳይሬክተርና አሁንም የትምህርት ስልጠና ዘርፍ ኅላፊ ነው። የወያኔ ደህንነት ኅይልን ጥቅምና አቅም እንዲያስጠብቅ በምስጢር የኢትዮጵያ ዐቃቤ ሕግ ምክትል ሆኖ ያለገለገለ ሰው ነው። አቶ መዝሙር ከገቢዎች ዐቃቤ ሕግ የመጣ ስውር ደህንነት ነው።

10) አቶ ገ/ዮሐንስ ተክሉ፣ ለረዥም ጊዜ የውጭ መረጃ ዳይሬክተር ሆኖ የሠራ፤ አሁን የኢሜግሬሽን ዳይሬክተር፤

11) አቶ መኮንን ( ወዲ ኮበል) ለረዥም ጊዜ የቤተ መንግስር የጥበቃ ደሕንነት የነበረ፣ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ ጥበቃና ደህንነት ውስጥ 99 በመቶ የህወሓት አባላት ላይ ኔትወርክ የነበረው ሰው ነው፤

12) አቶ ሰለሞን (ወዲ ትግራይ) የቴክኒክ የስልክ ጠለፋ ዋና ዳይሬክተር እና በተለይም የአማራና የኦሮሞ ተፅዕኖ ፈጣሪ ፖለቲከኞች፣ ምሁር፣ ባለሀብት ወዘተ. የተቋሙን ስምሪት ተጠቅሞ በድብቅ ለህወሓት ሲሠራ የነበረ፤

13)አፅብሓ የክትትል መምርያ ዳይሬክተር፤

14) አቶ መድህኔ ታደሰ:- የኢኮኖሚ መምርያ ኅላፊና ቀደም ብሎ የፖለቲካ ፓርቲዎች ክትትል ኃላፊ የነበረ፣ ማንኛውንም ከህወሓት የተቃረነ ጠላት ብሎ የሚጠራ፤

15)አማኑኤል ኪሮስ፣ የሀገር ውስጥ ዋና ዳይሬክተር እና በ2010 አጋማሽ የፀረ ሽብር ዋና ዳይሬክተር የሆነ፣ የወልቃይት ሕዝብን ላይ የተፈፀመውን ወንጀል እንደመራ ይገለፃል፣ የቅማንት ሴራ ላይ በድብቅ የተሳተፈ፣ አሁንም ህወሓት እንደዋና ሰንሰለት የሚጠቀምበት። በተለይ በወልቃይት፣ ከአማራና ቅማንት እያሉ የሚፈጥሩትን ክፍፍል ሲመራ የነበረ ሰው ነው።

16) ደርበው ደመላሽ (ጎጃሜው) የተሻለ አቋም ነበረው የሚባል ቢሆንም በሙስና በመዘፈቁ ምክንያት ጌታቸው አሰፋ ሲጠቀምበት የነበረ ሰው፤

17) ቢኒያም ማሙሸት:- በኢህአዴግ ካድሬነቱ የሚታወቅ፣ የኢህአዴግ በስልጣን መቆየት የህልውና ጉዳይ ነው ብሎ የሚያስብ ሰው ነው። “የአመፅ ኅይሎች ኦፕሬሽን” ኅላፊ የነበረ ሲሆን በተለይ አርበኞች ግንቦት 7 ላይ አተኮሩ የሚሰራ ነው። የአቶ አንዳርጋቸውን ምርመራ የሠራ ሲሆን፣ ከእሱ ጋር የአቶ አንዳርጋቸውን ምርመራ አብረው የሰሩት ሸዊት፣ ተወልደ፣ ብሩክ፣ ሲሳይ፣ ተስፋማርያም፣ ቴዎድሮስ ቦጋለ (አሁን ኢሜግሬሽን የሚሰራ)፣ ይልማ (ጅማ) የሚባሉ የህወሓት አባላት ናቸው።

18) ነብዩ (እስቴ) አሁን የፀረ ስለላ መምርያ የሆነ፤

19)ፍቃዱ ዓለማየሁ (ወዲ መርሳ) የኢኮኖሚ ደሕንነት በተለይ በሙስና የሚታወቅ እና በማዕከላዊ ምርመራ የሚሳተፍ፤

20) ኅይለማርያም ገብሩ እጅግ ዘረኛና ለሕወሓት የበላይነት የሚሰራ፣ ለጌታቸው አሰፋ፣ ለኢሳያስ ገ/ጊዮርጊስ በድብቅ መረጃዎችን የሚያቀብል፣ በ2010 አጋማሽ አንዲት ተዋናይ ያገባ፣ በሙስና እጁ የተጨማለቀ ሰው ነው።

21) ቴዎድሮስ ኃይሌ ከኅይለማርያም ገብሩ እና ከአማኑኤል ኪሮስ ጋር ተመሳሳይ ታሪክ ያለው።

22) ተመስገን ተክሉ ከወያኔ ኃይል ክንፍ አንዱ ነው። ቀደም ብሎ የኢትዮጵያ የክትትል ኅላፊ የነበረ ቀጥሎም የሀገር ውስጥ ደህንነት የሞብላይዜሽን ኅላፊ እና አሁን በዋና ተቋሙ የኦፕሬሽን ሞብላይዜሽን ኅላፊ በክፉነቱ የሚታወቅ ነው።

23) ጎህ አፅብሓ፣ የወያኔ ኃይል ደሕንነት መሥሪያ ቤቱ በአዲስ አበባ ዋና ኅላፊና የክልሎች ማስተባበሪያን ምክትልና የሰሜን ምስራቅ፣ የምስራቅ ኢትዮጵያ አስተባባሪም ነው። በተለይ በአዲስ አበባ የተፎካካሪ ፓርቲዎችን ጌታቸው በሚሰጠው ተልዕኮ ሴራ እያደራጀ ይሠራ የነበረ ሰው ነው።

24) አሰፋ በላይ የወያኔው ኅይል አካል ነው። መደበኛ ስምሪት በክልሎች መምርያ የአፋር ክልል የደህንነት ስምሪት ኅላፊ በስሩ ሌሎች 10 ደሕንነቶች ይመራል። ባለፉት ዓመታት ተፈጥረው የነበሩትን የወሎና የአፋር ግጭቶች ላይ እጁ እንዳለበት ይነገራል። የአፋርና ከረዩ፣ የሶማሊና አፋር ግጭት ላይም እጁ እንዳለበት ይነገራል።

25) እንግዳው፣ ዋና መቀመጫውን ባህር ዳር ላደረገው የአማራ ክልል የደህንነት ስምሪት ዋና ኅላፊ ነው።

ከአራትና አምስት ዓመታት በፊት በአዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ ደህንነት የነበረ ሲሆን፣ 10ኛ ክፍል ጅምሮ በመከላከያ ሠራዊቱ ውስጥ እያስተማሩ ያሰሩት እና በአማኑኤል ኪሮስ፣ ጎሕ አፅብሓ እየተመራ የክልሉን ሁኔታ ለወያኔ የሚሰጥ ነው። ወያኔ በቤንሻንጉል፣በአፋር፣ የአማራና ቅማንት ድራማ፣በወልቃይት የሚደርሰው ግፍ እጁ እንዳለበት ይገለፃል።

በእንግዳው ስር የሚታዘዙ፤

1)አቶ አሸናፊ ተስፋሁን:- የሰሜን ጎንደር ዞን ደሕንነት ኅላፊ የህወሓትን የበላይነት ለማስቀጠል ታዛዥ የሆነ ቅማንትና አማራን በማፋጀቱ ወዲ ቅማንት ብለው የሚጠሩት ሲሆን ጎንደር ብልኮ ከሚገኘው ቢሮ ብዙ የአማራ ወጣቶች ላይ ስቃይ እንዲፈፀምበቸው ያደረገ ሰው ነው። የአማራ ወጣቶችን ለትግራይ ክልል ፀጥታና ደሕንነቶች አሳልፎ የሚሰጥ ሰው ነው። በስሩም ታደሰ ደርሶ፣ ደርሶ አያና፣ ታምራት፣ መንበረ፣ የሚባሉ እስከ 10 የሚደርሱ የደህንነት አባላት አሉት።

2)ብሩክ፣ የደቡብ ጎንደር ዞን የደህንነት ምድብ ኅላፊ ነው። የሚኖረው ደብረ ታቦር ነው። ከአሁን ቀደም በአካባቢው ለተፈፀሙ በደሎች እጁ አለበት ተብሎ የሚወቀስ፣ በ2010 ዓ.ም. ዶ/ር ዐቢይ መመረጥ በኋላም ደብረታቦር ውስጥ ስብሰባ ተደርጎ ወያኔ የሚፈፅመውን ወንጀል ያጋለጡትን በማፈንና በማሰቃይት የሚታወቅ ሰው ነው።

3) ሙሉ ጎጃም፣ የምሥራቅና ምዕራብ ጎጃም ደህንነት አስተባባሪ ነው። ወደ ኢትዮጵያ ሀይል ያመዘነ ሲሆን ከአሁን ቀደም ብዙ ጥፋቶች ፈፅሟል።

4) በቀለ፣ የደቡብ ወሎ ዞን፣ የሸዋ (ደብረብርሃን) ጭምር አስተባባሪ ነው። ቀደም ብሎ የአዲስ አበባ ደሕንነት ስምሪት የአቃቂ የደህንነት ኃላፊ ነበር። ቀደም የወያኔ ኅይል የነበረ ሲሆን አሁን ወደ ኢትዮጵያ ኅይል እየመጣ ነው ተብሏል።

5) አቶ በርሄ እና አቶ ሐየሎም የሰሜን ወሎ ዞን እና የደቡብ ትግራይ የሚሉት የደሕንነት ስምሪት ኅላፊዎች ናቸው። ለቀጠናው የወያኔ ልዩ ትኩረት የተነሳ በቀጥታ እራሳቸው ከህወሓት ጋር እየተጠረነፉ ይሰራሉ። በተለይ በአካባቢው ያለውን የራያ፣የአላማጣ፣ የማይጨው፣ የራያ ቆቦ፣ በመሆኑ ወዘተ የአማራ ክልልና ብሔር ማንነት ጥያቄ እንዳይደራጅ በመነጣጠል፣ በማፈን፣ እየሰሩ ያሉ አሁንም በትግራይ ታፍነው የአማራ ልጆች የሚለቅሙ ናቸው።

26) አቶ ገብረ እግዚያብሔር (ገሬ)፣ አቶ ገብረ መድህን በኢትዮጵያ ሶማሊ እና እስከ ሀረርጌ፣ ቶጉጫሌ ባለው ቀጠና የደሕንነት ሀላፊዎች ሲሆኑ ህወሓት እንደፈለገ እየተጠቀመበት ያለ አካባቢ ነው። በጌታቸው አሰፋ የሚታዘዙ ናቸው። ከሁለቱ ደህንነቶች ጋር በቅንጅት የሚሠሩ ናቸው።

የወያኔ ኅይል ተብሎ የሚታወቀው የደሕንነት መሩሪያ ቤቱ ኅይል ከጀኔራል አብርሃ፣ ጀኔራል ዮሐንስ፣ ዓባይ ፀሐዬ፣ ከሶማሊ ክልል ፕሬዝደንት አብዲ ኤሊ፣ ሀዋ መሐመድ ጫት ላኪ ናት እና ከሌሎችም ጋር በጥቅም ትስስር የሚሠራ ነው። የዶክተር ዐቢይ አሕመድ መንግሥት ወደ ሥልጣን ከመጡ በኋላ የደሕንነት መሥሪያ ቤቱን ለትህነግ/ህወሓት ሥልጣንና ለግል ጥቅሙ የሚያውለው የወያኔ ኅይል በሕግ እንዲጠየቅ እያደረገ ሲሆን የደህንነት መሥሪያ ቤቱ ካሉት አባላት መካከል እስከ 3000 የሚደርሰው በጌታቸው አሰፋ ይመራ በነበረው የወያኔ ኅይል ከመሆኑ አንፃር አሁንም የደህንነት መሥሪያ ቤቱን ለትህነግ/ህወሓት ሥልጣንና ለግል ጥቅም ከሚያውሉት ለማፅዳት ረዥም ርቀት መሄድ እንደሚገባ አመላካች ነው።