አፋር ክልል በሕወሓት የከባድ መሣሪያ ጥቃት 10 የአንድ ቤተሰብ አባላት መገደላቸውን ተሰማ።

አፋር ክልል ሕወሓት በተኮሰው ከባድ መሣሪያ ጥቃት 10 የአንድ ቤተሰብ አባላት መገደላቸውን ተሰማ።

ጦርነት ተባብሶ በቀጠለበት የአፋር ክልል ነዋሪ የሆኑት አቶ ሁሞ ኢብራሂም ከቀናት በፊት በተፈጸመ የከባድ መሳሪያ ጥቃት ሚስታቸውንና 5 ልጆቻቸውን አጥተው እጅግ ከባድ ሐዘን ውስጥ እንደሚገኙ ቢቢሲ ዘግቧል።

ቢቢሲ በጎ ፈቃደኞችንና ከአካባቢው የወጡ ሰዎችን በማነጋገር በሰራው ዘገባ ባለፈው ማክሰኞ የካቲት 8 ምሽት በተፈፀመ የከባድ መሳሪያ ጥቃት 10 የአንድ ቤተሰብ አባላት ተገድለዋል።

በጥቃቱ 10 የቤተሰብ አባሎቻቸው የተገደሉባቸው አቶ ሁሞ እና ቤተሰባቸው ይኖሩ የነበረው ‘አዳ’ የምትባል ትንሽ ከተማ ነበር።

ከተማዋ ከበርሃሌ 15 ኪ.ሜ ርቀት ላይ የምትገኝ እንደሆነች በሰመራ ነዋሪ የሆኑት የአቶ ሁሞ የቅርብ ዘመድ አቶ ያሲን ከድር ገልፀው አጠቃላይ ዘመድ በከባድ ሐዘን ውስጥ መሆኑን ተናግረዋል።

በጥቃቱ ልጆቻቸውን ይዘው በመሸሽ ላይ ከነበሩት የቤተሰብ አባላት መካከል 5 ህጻናት፣ እናት፣ የእናት እናት [አያት]፣ የእናት ወንድምና የአባት እህት 2 ልጆች መሆናቸው ተገልጿል።

አባወራው አቶ ሁሞ ቀድመው ከአካባቢው ተፈናቅለው ወጥተው ስለነበር በቤተሰባቸው ላይ ከደረሰው አደጋ ሊተርፉ ችለዋል። ሙሉ ቤተሰባቸውን ያጡት አባት ሐዘኑን ሊቋቋሙ በማይችሉት ሁኔታ ውስጥ ይገኛሉ።

“ምግብ አይበሉም። እንደ ድንገት የወረደባቸውን መዓት መቋቋም አልቻሉም። የሃይማኖት አባቶች እያጽናኑዋቸው ነው” ሲሉም ከባድ የሃዘን ስሜት ላይ መሆናቸውን አቶ ያሲን ተናግረዋል።

ቢቢሲ አቶ ሁሞን ለማነጋገር ጥረት ቢያደርግም በደረሰባቸው መሪን ሐዘን ምክንያት ከማንም ጋር እንደማይነጋገሩ ዘመዶቻቸው መግለፃቸውን በዘገባው ጠቅሷል።

ከሟቾች በተጨማሪ 13 ሰዎች የከፋ ጉዳት ደርሶባቸው ዱብቲ ሆስፒታል ይገኛሉ።