የመንግስት ድሮን በትግራይ ወፍጮ ቤት እህል ለማስፈጨት በተሰበሰቡ ሰዎች ላይ ጥቃት ፈፅሟል ተባለ

እንደ አውሮፓውያን የቀን አቆጣጠር ኅዳር 22/2021 ዓ.ም በፕላኔት ላብ የተወሰደውና ፓክስ የተሰኘው ተቋም ያሰባሰበው ይሄ የሳተላይት ምስል መረጃ ዊንግ ሎንግ' የተሰኙ ቻይና ሰር ሰው አልባ አውሮፕላኖች የኢትዮጵያ የአየር ኃይል መቀመጫ በሆነው በቢሾፍቱ ሐራሜዳ ላይ ቆመው ይታያሉ። /ፕላኔት ላብ ፒቢሴስ/ ኤኤፍፒ/ VOA : በኢትዮጵያ እየተካሄደ ባለው ጦርነት ዋና የውጊያ መሳሪያ ሆነው ጥቅም ላይ እየዋሉ ባሉት ሰው አልባ ወታደራዊ አውሮፕላኖች (ድሮኖች) በቅርቡ ጥቃት ከደረሰባቸው ሰዎች መሀከል በወፍጮ ቤት ውስጥ የሚሠሩ ሠራተኞች ናቸው።

ጥር 2/2014 ዓ.ም በትግራይ ክልል፣ ማይ ፀብሪ ከተማ በደረሰው ጥቃት ጉዳት ከደረሰባቸው 17 ሰዎች ውስጥ አብዛኞቹ ሴቶች ሲሆኑ የዐይን እማኞች ሰው አልባ የሆነ የአየር ላይ ተሽከርካሪ እህል ለማስፈጨት በተሰበሰቡ ሰዎች ላይ ጥቃት እንዳደረሰ ተናግረዋል።

“ሰው አልባ አውሮፕላኑ መጥቶ ትንሽ ካንዣበበ በኋላ ቦምብ መጣል እንደጀመረ አንድ የአይን እማኝ ነግሮኛል። ከዛ ሰዎች መደናገጥ ጀመሩ። ከጥቂት ደቂቃ በኋላ ጩኸት የሰሙ ሰዎች ወደ ቦታው ሲሄዱ ሴቶች እና አህያዎች ሞተው አገኟቸው።” ሲል አንድ የእርዳታ ሰራተኛ ለአዣንስ ፍራንስ ፕሬስ ተናግሯል።

ከታኅሣሥ አጋማሽ ወዲህ የኢትዮጵያ አየር ኃይል በትግራይ ክልል ላይ ባደረሰው ጥቃት እስካሁን ቢያንስ 108 ንፁሃን ዜጎች መገደላቸውን የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት አስታውቋል። የተወሰኑት ጥቃቶችም ስደተኞች እና ተፈናቃዮች የሚገኙባቸው መጠለያ ጣቢያዎችን ኢላማ ያደረጉ እንደነበርም የመንግሥታቱ ድርጅቱ ጨምሮ ገልጿል።

በዚህ 15 ወራትን ባስቆጠረው ጦርነት በውጪ ሣገራት የተሰሩ ሰው አልባ አውሮፕላኖች፣ የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስቴር የትግራይ ተዋጊዎችን ጥቃት እንዲቀለብሱ ቢያስችላቸውም፣ በንፁሃን ዜጎች ላይ የደረሰውን ጥቃት ግን በርካቶች አውግዘዋል። የታጠቁ ሰው አልባ አውሮፕላኖች የሚፈጥሩትን ምሳሌም ጥያቄ ውስጥ እንዲከቱ አድርጓቸዋል።

ዊም ዝዊጀምበርግ ፓክስ በተሰኘ ዓለም አቀፍ ግጭቶችንና የጦር ቴክኖሎጂ አጠቃቀም በሚያጠና የኔዘርላንድ ድርጅት ውስጥ፣ ሰብዓዊ የጦር መሳሪያ ቅነሳ ፕሮጀክት አመራር ሲሆኑ ኢትዮጵያ ወታደራዊም ሆነ ሌላ የሀገር ውስጥ ችግሯን ለመፍታት ሰው ሰራሽ አውሮፕላኖችን ወይም ድሮኖችን መጠቀሟን ሌሎች ሀገሮችም ሊከተሉ ይችላሉ የሚል ስጋት አላቸው።

ዝዊጀምበርግ ከአሜሪካ ድምፅ ጋር በምስል ባደረጉት ቃለምልልስ “ሰው አልባ አውሮፕላኖች በቀጠናው ጥቅም ላይ መዋላቸው አሳሳቢ የሚያደርገው፣ በተለይ የትጥቅ ትግል በሌለበት ሁኔታ፣ የጦር መሳሪያ አጠቃቀም ዙሪያ ያለውን መሰረታዊ ሁኔታ የሚያወርደው በመሆኑ ነው። ያ ደግሞ በጣም ያሳስባል፣ ምክንያቱም እንደዚህ አይነት መንገዶች ውስብስብ የሆኑ ጉዳዮችን በቀላሉ መፍቻ ዘዴ ተደርገው ሊታዩ ይችላሉ” ይላሉ።

ናይጄሪያን ጨምሮ ሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ሰው አልባ አይሮፕላኖችን ለውጊያ ይጠቀሙባቸዋል። እንደ ዩናይትድ ስቴትስና ፈረንሳይ ያሉ ሀያላን ሀገራትም አፍሪካ ውስጥ በሽብር የተጠረጠሩ ቡድኖች ላይ በሰው አልባ አውሮፕላን ጥቃት አካሂደዋል። ባለሞያዎች እንደሚሉት ግን በኢትዮጵያ እየተካሄደ ባለው ጦርነት ጥቅም ላይ የዋለበት መንገድ ግን አንድ እርምጃ የተሻገረና ሌሎች ሀገራትም ቴክኖሎጂው እንዲኖራቸው የጦር እሽቅድድም ውስጥ እንዲገቡ የሚያደርጋቸው ነው ብለው ይሰጋሉ።

የኢትዮጵያ መንግሥት ጦርነቱ ከተጀመረ ጀምሮ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን መጠቀሙን በሚስጥር የያዘው ጉዳይ አይደለም። እንደውም በርቀት ጥቃቶችን ማድረስ የሚያስችል አቅም ያለው መሆኑን ለማሳየት ተጠቅሞበታል። የኢትዮጵያ አየር ኃይል አዛዥ ሌተናንት ጀነራል ይልማ መርዳሳ በሕዳር ወር ለመንግሥት ሚዲያ ሲናገሩ “አሁን ቁልፍ በመጫን ብቻ መዋጋት የምንችልበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው” ብለው ነበር። “ቢሮአችን ቁጭ ብለን፣ የምንፈልገውን ቁልፍ በመጫን፣ ኢላማችንን ማስወገድ እንችላለን። የአየር ሀይላችንን በዚህ መልኩ እየገነባነው ነው።” ብለዋል።

በትግራይ ክልል የመገናኛ መንገዶች ሁሉ ቢቋረጡም፣ እንደ ዝዊጀምበርግ ያሉ ዓለም አቀፍ ባለሞያዎች ግን ምን ዓይነት ሰው አልባ አውሮፕላኖች የት ቦታ ጥቅም ላይ እንደዋሉ ለማረጋገጥ ተጨባጭ ማስረጃዎችን ሲያፈላልጉ ቆይተዋል። በተለይ ሰው አልባ አውሮፕላኖቹ የመቆሚያ ጣቢያቸው የት እንደሆነ እና፣ የተባበሩት አረብ ኤምሬትስ በየመን ከሚገኙት የሁቲ አማፂያን ጋር ለሚያደርገው ጦርነት የጦር ሰፈሩን ከገነባበት፣ የጎረቤት ሀገር ኤርትራ ይንቀሳቀስ እንደሆነ ለማወቅ ጥረት አድርገዋል።

ባለሞያዎቹ ከሳተላይት የተወሰዱ ፎቶዎችን እና በእጅ ስልኮች የተነሱ የቪዲዮ ምስሎችን የመረጃ ክፍተቶችን ለመሙላት የተጠቀሙባቸው ሲሆን፣ ፓክስ የተሰኘው ተቋም ከሳተላይት ምስሎች ባገኘው መረጃ መሰረት፣ ስድስት ኢራን ሰራሽ የሆኑ ‘ሞሀየር’ የተሰኙ ሰው አልባ አውሮፕላኖችንና ‘ዊንግ ሎንግ’ የተሰኙ ቻይና ሰር ሰው አልባ አውሮፕላኖችን የኢትዮጵያ የአየር ኃይል መቀመጫ በሆነው ሐረር ሜዳ ላይ ቆመው ማየት ችለዋል። በቱርክ የተሠሩ ቲ-ቢ-ቱ የተሰኙ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ደግሞ በአማራ ክልል፣ ባህር ዳር ከተማ መቆማቸውንም መለየት ችለዋል።

ሰው ሰራሽ አውሮፕላኖች ላይ መሰረት ያደረገ ዲፕሎማሲ

ቤሊንግ ካት የተሰኘ እውነተኛ መረጃዎችን የሚያጣራ ድህረገፅ ያወጣው መረጃ እንደሚያሳየው፣ ኢራን ሰው ሰራሽ አውሮፕላኖችን እና መገጣጠሚያዎችን ሽያጭ እንደ ኢራቅ፣ ሊባኖስ፣ የመን እና የጋዛ ሰርጥ ካሉ ሀገራት ጋር ያላትን ግንኙነት ለማጠናከር ትጠቀምበታለች። ዝዊጀምበርግ ኢትዮጵያ አሁን ከነዚህ ሀገራት ዝርዝር ውስጥ መካተቷን የሚያሳይ መረጃ አለ ይላሉ። እንደማስረጃም በክረምት ወራት ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡና የሚወጡ የኢራን አውሮፕላኖች ቁጥር መጨመርን ይገልፃሉ። ከነዚህ ውስጥ አንዱ በረራ በዩናይትድ ስቴትስ የግምጃ ቤት ማዕቀብ ከተጣለበት የኢራን መንግሥት ጋር ግንኙነት ያለው መሆኑንም ይጠቁማሉ።

ይሄ እንደ አዎሮፓውያን አቆጣጠር በታኅሣስ 9/2021 ዓ.ም በሳተላይት የተወሰደው ፓክስ የተሰኘው የኔዘርላንድ ተቋም የተወሰደው ምስል በቱርክ የተሠሩ ቲ-ቢ-ቱ የተሰኙ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ደግሞ ቢሾፍቱ ከሚገኘው ሰሜናዊ የአየር ማረፊያ ሃራ ሜዳ ውጪ ቆሞ ይታያል። /ፕላኔት ላብ ፒቢሴስ/ ኤኤፍፒ/
ይሄ እንደ አዎሮፓውያን አቆጣጠር በታኅሣስ 9/2021 ዓ.ም በሳተላይት የተወሰደው ፓክስ የተሰኘው የኔዘርላንድ ተቋም የተወሰደው ምስል በቱርክ የተሠሩ ቲ-ቢ-ቱ የተሰኙ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ደግሞ ቢሾፍቱ ከሚገኘው ሰሜናዊ የአየር ማረፊያ ሃራ ሜዳ ውጪ ቆሞ ይታያል። /ፕላኔት ላብ ፒቢሴስ/ ኤኤፍፒ/

ዝዊጀምበርግ “ላለፉት አመታት በሰሜን አፍሪካ እና በመካከለኛው ምስራቅ ለሚገኙ መንግሥታዊም፣ መንግሥታዊ ያልሆኑም አካላት ሲልኩ ነበር” ይላሉ። “እናም ምንም እንኳን መረጃዎቹ የተሟሉ ባይሆኑም፣ ከሰው አልባ አውሮፕላኖቹ ቅርፅ፣ መጠን፣ መሳሪያው እና በምስሎቹ ላይ የሚታዩት የመሬት ላይ መቆጣጠሪያ ጣቢያዎቹ በመነሳት፣ ሰው አልባ ወታደራዊ አውሮፕላኖቹ ኢራን ሰራሽ መሆናቸውን አመላካች ነው።”

ሰው አልባ አሮፕላኖች ገበያ ላይ ቱርክም ዋና ተዋናይ ናት። አል ሞኒተር የተባለው የዜና አውታር እንደዘገበው ቱርክ 13 ቤይራክታር ቲ-ቢ-ቱ የተሰኙ ሰው አልባ አውሮፕላኖች ለኢትዮጵያ ሸጣለች። ጠቅላይ ሚኒስቴር አብይ አህመድ ከቱርክ ፕሬዝዳንት ሪሴፕ ታይፕ ኤርዶጋን ጋር በነሐሴ ወር ተገናኝተው የወታደራዊ ትብብር ሥምምነት ከተፈራረሙ በኋላ ቱርክ ሰራሽ ሰው አልባ የአየር ተሽከርካሪዎችም መታየት ጀመሩ።

የቱርክ መከላከያ እና አየር ኃይል ኢንዱስትሪ በድህረ ገፁ ላይ ባወጣው መረጃም ቱርክ 51.7 ሚሊየን ዶላር የሚያወጣ ምርት ወደ ኢትዮጵያ መላኩን አመልክቷል። የአሜሪካ ድምፅ ራዲዮ የሰው አልባ አሮፕላኖቹን ግዢ እና አጠቃቀም በተመለከተ መረጃ ለማግኘት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ቢሮ እና ቃል አቀባያቸው ቢልለኔ ስዩም በተደጋጋሚ በኢሜል ጥያቄ ቢያቀርብም ምላሽ አላገኘም።

ባለሞያዎች ቱርክ ሰው አልባ ወታደራዊ አሮፕላኖችን ለሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ለመሸጥ ታስባለች የሚል ስጋት አላቸው። ቱርክ በአሁኑ ሰዓት ከ25 የአፍሪካ ሀገራት ጋር የወታደራዊ ትብብር ስምምነት ያላት ሲሆን ለሞሮኮም ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ሸጣለች።

ባሳለፍነው ክረምት አፍሪካን ጎብኝተው የነበሩት ኤርዶጋንም ሌሎች ሀገራትም የጦር ቴክኖሎጂውን ለማግኘት ስላላቸው ፍላጎት በኩራት ተናግረው ነበር። ኤርዶጋን በጥቅምት ወር ቢካር የተሰኘውን የቱርክ ሰው አልባ አውሮፕላኖች ማምረቻ ፋብሪካ በጎበኙበት ወቅት “በየሄድኩበት፣ የአፍሪካ ሀገራት ስለ ሰው አልባ ወታደራዊ አውሮፕላኖች ይጠይቁኛል” ማለታቸውን አል-ሞኒተር ዘግቧል።

የሰው ሰራሽ አውሮፕላኖች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ መጨመር፣ መሳሪያዎቹ ያለምንም ገደብ በተቃዋሚዎች፣ መብት አቀንቃኞች እና የተገፉ ማኅበረሰቦች ላይ ጥቅም ላይ ይውላል የሚል ፍራቻ ባላቸው የፀጥታ ባለሞያዎች እና ሰብዓዊ መብት አራማጆች ዘንድ ሥጋት ፈጥሯል።

ይህ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በታኅሣሥ 2/2021 ዓ.ም በሳተላይት የተወሰደው ፓክስ የተሰኘው የኔዘርላንድ ተቋም የተነሳው ምስል ከኢራናዊው ሞሃጀር- 6 ጋር ተመሳሳይ ልኬት ያለው ሰው አልባ አውሮፕላn ደግሞ ቢሾፍቱ ከሚገኘው ሰሜናዊ የአየር ማረፊያ ሃራ ሜዳ አስፋልት ቆሞ ይታያል። /ፕላኔት ላብ ፒቢሴስ/ ኤኤፍፒ/
ይህ እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር በታኅሣሥ 2/2021 ዓ.ም በሳተላይት የተወሰደው ፓክስ የተሰኘው የኔዘርላንድ ተቋም የተነሳው ምስል ከኢራናዊው ሞሃጀር- 6 ጋር ተመሳሳይ ልኬት ያለው ሰው አልባ አውሮፕላn ደግሞ ቢሾፍቱ ከሚገኘው ሰሜናዊ የአየር ማረፊያ ሃራ ሜዳ አስፋልት ቆሞ ይታያል። /ፕላኔት ላብ ፒቢሴስ/ ኤኤፍፒ/

የኢትዮጵያን የሰው አልባ አውሮፕላን አጠቃቀም በተመለከተ በመስከረም ወር ላይ ጥያቄ ቀርቦላቸው የነበሩ አንድ የዋይት ኋውስ ባለሥልጣን ምላሽ ሲሰጡ፣ ሁኔታው ጦርነቱን ለማስቆም የሚደረገውን ጥረት እንዳወሳሰበው ገልፀው ነበር።

ባለሥልጣኑ ከጋዜጠኞች ጋር በነበራቸው ቆይታ “የመሳሪያ ክምችት መጨመር ኢትዮጵያን አያረጋጋትም። እንደውም ያ ኢትዮጵያኖች ያላቸውን ቅሬታ ያባብሰዋል። ጠቅላይ ሚኒስቴር ዐቢይ እራሳቸው ለኢትዮጵያ ወደአስቀመጡት የብልፅግና ግብ የሚወስድም አይደለም” ሲሉ ተናግረው ነበር።

ዝዊጀምበርም ተመሳሳይ ሥጋት ነው ያላቸው።

“ሰው አልባ አውሮፕላኖች አፍሪካን ጨምሮ በብዛት ወደ ውጪ በተላኩ እና በተከማቹ ቁጥር ዋና ሥጋታችን በርካታ የአፍሪካ ሀገራት ይሄንን ሰው አልባ ወታደራዊ አውሮፕላኖችን እንደ አንድ መንገድ መጠቀም ይጀምራሉ የሚለው ነው” ይላሉ። “የሀገር ውስጥ ወታደራዊ እንቅስቃሴን ለመግታት የሚደረግ ጥረትም ቢሆን፣ አፍሪካ ህብረትን ጨምሮ ሁሉም የአፍሪካ ሀገራት ሊፈቱት የሚገባ ችግር ይመስለኛል። ይህን ሥጋታቸውን እየገለፁ ያሉ በአፍሪካ የሚገኙ በርካታ የሲቪል ማኅበራት እና የህግ ባለሙያዎችም አሉ።”

ዘገባው የተጠናቀረው በሳሌም ሰለሞን ነው።