የቀድሞው የደህንነት ሃላፊ ጌታቸው አሰፋ የሀዋሳውን ጉባኤ ይታደማሉ? አቶ ጌታቸው ረዳን በስልክ አነጋግረናቸው ነበር – BBC Amharic

ለመኾኑ አቶ ጌታቸው አሰፋ ወደ ሥራ አስፈጻሚ መምጣታቸው አሁን ባለው የለውጥ አውድ ምን ፖለቲካዊ ትርጉም ይሰጣል?

በጉዳዩ ላይ አስተያየታቸውን እንዲሰጡን የህወሓት የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል እና የቀድሞ የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ቢሮ ኃላፊ የነበሩትን አቶ ጌታቸው ረዳን በስልክ አነጋግረናቸው ነበር።

”ጌታቸው አሰፋ ጎበዝ መሪ መሆኑን አውቃለሁ። ጎበዝ ኢህአዴግ መሆኑን አውቃለሁ። ጎበዝ ህወሓት መሆኑን አውቃለሁ። ህወሓት ሲወስን በሚዲያ ሃሜት ላይ ተመሥርቶ አይደለም የሚወስነው” በማለት በቀድሞው የደኅንነት ሹም አቶ ጌታቸው አሰፋ ላይ የሚቀርቡ ወቀሳዎችን አጣጥለዋል።

አቶ ጌታቸው ጨምረውም ”ይፋዊ መግለጫ ሳይኖር ሚዲያዎች ሃሜት ሲያወሩ ነበር። ሃሜት ላይ ተወስነን ውሳኔ የምናስተላልፍ ቢሆን ኖሮ ሃገር ይጠፋል። ክስ ስለመመስረቱም የማውቀው ነገር የለም። አቶ ጌታቸው አሰፋን ፈልጎ ህውሓት ጋር የመጣ አካል የለም።” በማለት አቶ ጌታቸው አሰፋ ላይ ክስ አለመመሥረቱን አመላክተዋል።

አቶ ጌታቸው አያይዘው እንደሚሉት ከሆነ አቶ ጌታቸው አሰፋ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ሆኖ የመመረጥ ፍላጎት አልነበራቸውም። ”ማዕከላዊ ኮሚቴ ውስጥ መግባትም አልፈለገም፤ ሲሪየስሊ [አጥብቆ] ነው የተከራከረው። ጉባኤው ግን ከማዕከላዊ ኮሚቴ ውስጥ እንዲገባ ወሰነ። ማዕከላዊ ኮሚቴው ደግሞ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል ውስጥ መግባት አለበት ብሎ ወሰነ።” ይላሉ አቶ ጌታቸው ረዳ።

“አቶ ጌታቸው አሰፋ በጉባኤው ላይ ለመሳተፍ ወደ ሀዋሳ ይሄዳሉ ወይ?” ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ አቶ ጌታቸው ረዳ ሲመልሱ ”የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል በጉባኤው እንዲሳተፍ ይጠበቃል። እንደማንኛው የኮሚቴ አባል ሀዋሳ ላይ ልታይዋቸው ትችላላችሁ። እንደማንኛውም የማዕከላዊ ኮሚቴ አባል ተሳትፎ ማድረግ ስላለብን አንዳንዶቻችን ያው መንገድ ላይ ነን። ለምሳሌ አውሮፕላን ካመለጠኝ ልቀር እችላለሁ” ብለዋል።

ይህ አገላለጽ ‘አቶ ጌታቸው አሰፋ ላይገኙ ይችላሉ’ የሚለውን ያመላክት እንደሆነ ከቢቢሲ የተጠየቁት አቶ ጌታቸው ረዳ፣”እኔ የእያንዳንዱ ሰው ስኬጁል አላወጣም። ሁላችንም ተበትነን ነው ወደ ሀዋሳ እየሄድን ያለነው፤ ጌታቸውም በራሱ ጊዜ ስኬጁሉን አሬንጅ ያደርጋል፤ ካገኘሁት እነግራችኋለሁ” ሲሉ በቀልድ የታጀበ ምላሽ ሰጥተዋል።

ነገ በሚጀመረው የኢህአዴግ 11ኛ ድርጅታዊ ጉባኤ ላይ የድርጅቱ ሊቀ መንበር ማን ሊሆን ይችላል ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ ”አሁን ያሉት ሊቀ መንበር ላለፉት 5 ወይም 6 ወራት ሲያገለግሉ ቆይተዋል። እስካሁን የሠሩት ሥራ ተገምግሞ ለውጥ ማድረግ ያስፈልገናል ወይስ አያስፈልገንም የሚለው የጉባኤው ውሳኔ ነው የሚሆነው” በማለት መልሰዋል።

ህወሓት ማንን በእጩነት ለማቅረብ እንደተሰናዳ የተጠየቁት አቶ ጌታቸው ረዳ ፓርቲዎች እንደማይመርጡ አስረድተዋል። ”ህወሓት፣ ብአዴን ወይም ኦህዴድ ዕጩዎችን አያቀርቡም። ፓርቲዎች አይደሉም ዕጩዎችን የሚጠቁሙት። ከ180ዎቹ የኢህአዴግ ምክር ቤት አባላት ግለሰቦችን ለሊቀ መንበርነት ለጉባኤው ጥቆማዎችን ይሰጣሉ። ከዚያም ምርጫ ይካሄዳል። ድምጽ ያገኘ ያሸንፋል።” ብለዋል።

በግንባሩ ጉባኤ ላይ ሊነሱ የሚችሉ ዋና ዋና ጉዳዮች ምን ሊሆኑ እንደሚችሉ የተጠየቁት አቶ ጌታቸው፤ ”የዕድገት እና ትራንስፎርሜሽን ዕቅዱ አፈጻጸም ላይ መቀዛቀዝ ይታያል። ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት እሱን እንዴት አድርገን ነው በፍጥነት የምናስቀጥለው የሚለው ትልቁ አጀንዳ ነው። ወደ ሃገር እንዲገቡ የተደረጉ ተፎካካሪ፣ ተቃዋሚ የሚባሉ ፓርቲዎች ወደ ሃገር ከገቡ በኋላ አንዳንዱ ‘አሸንፌ ነው የመጣሁት’ ይላል። ሌላኛው ‘ወደሽ ሳይሆን ተገደሽ ነው የተቀበልሺኝ’ ይላል። ይህ ዓይነት ስሜት የሚፈጥረው የሰላም እና የመረጋጋት ዝብርቅርቅ አለ። ይህን ለመሰሉ ጉዳዮች ጉባኤው ምላሽ ይሰጣል። ይህ የሁላችንም አጀንዳ ነው” ብለዋል።

የኢትዮጵያ ሕዝቦች አብዮታዊ ዴሞክራሲያዊ ግንባር (ኢህአዴግ) 11ኛ ድርጅታዊ ጉባኤውን ከነገ ጀምሮ በሀዋሳ ያደርጋል። አራቱ የኢህአዴግ እህት ድርጅቶችም ከድርጅታዊ ጉባኤው በፊት የፓርቲዎቻቸውን ሊቀ መንበር፣ ምክትል ሊቀ መንበር፣ የማዕከላዊ እና የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት ምርጫን አካሂደዋል።

የኦሮሞ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ድርጅት (ኦህዴድ) መጠሪያውን ወደ የኦሮሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኦዴፓ) በተመሳሳይ መልኩ የብሔረ አማራ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) ደግሞ ወደ የአማራ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (አዴፓ) መቀየራቸው ይታወሳል። ሁለቱ ፓርቲዎች ከስማቸው ባሻገር የአርማ ለውጥም አድርገዋል።

በሌላ በኩል ሕዝባዊ ወያኔ ሃርነት ትግራይ (ህወሓት) እና የደቡብ ኢትዮጵያ ሕዝቦች ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ደኢህዴን) የቀድሞ ስማቸውን እና አርማቸውን ይዘው ቀጥለዋል።

ኦዴፓ፣ አዴፓ እና ዴኢህዴን በርካታ የቀድሞ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባሎቻቸውን በአዲስ እና ወጣት አባሎች ተክተዋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ ህውሓት ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል አድርጎ የመረጣቸው ግለሰቦች ነባር እና ከሞላ ጎደል የድርጅቱ ታጋዮች መሆናቸው አነጋጋሪ ሆኖ ቆይቷል። በተለይ ደግሞ የቀድሞው የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት ዋና ዳይሬክተር የነበሩት አቶ ጌታቸው አሰፋ ከዐሥራ አንዱ የድርጅቱ የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት መካከል አንዱ ሆነው መመረጣቸው ብዙዎች ህወሓት ከለውጡ ራሱን ገሽሽ እያደረገ ስለመሆኑ እንደ አንድ ማሳያ አድርገው ወስደውታል።