የ200 ሺህ ዶላር ተሸላሚ በመሆንዎ እንኳን ደስ አለዎት በሚል የማጭበርበር ስራ እየተሰራ መሆኑ ፖሊስ ገለጸ

በኮካ ኮላ ድርጅት ስም የ200 ሺህ ዶላር ተሸላሚ በመሆንዎ እንኳን ደስ አለዎት” በሚል የማጭበርበር ስራ እየተሰራ በመሆኑን ህብረተሰቡ ጥንቃቄ መድረግ እንዳለበት በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ወንጀል ኢንተለጀንስ አሳስበዋል፡፡

ድርጅቱ ለምርጥ ደንበኞቹ የሽልማት ፕሮግራም አዘጋጅቶ የነበረ እና ከተመረጡ ደንበኞች አንዱ እርስዎ ኖት በሚል ለተለያዩ ጉዳዮች ማስፈፀሚያ የሚሆን 640 ሺህ የኢትዮጵያ ብር ቶሎ ይላኩ እያሉ እንደሚያጭበረብሩ ኮሚሽኑ ገልጿል፡፡

ከዚህ የማጭበርበር ወንጀል ጋር በተያያዘ ተበዳዮች በተለያየ ጊዜና አካውንት 640 ሺህ የኢትዮጵያ ብር ለአጭበርባሪዎቹ ገቢ ካደረጉ በኋላ ደብዛቸውን እንዳጠፉባቸው ለኮሚሽኑ ተናግረዋል፡፡

ለአብነትም አንድ ተበዳይ ግለሰብ 92 ሺህ ብር በአጭበርባሪዎቹ አካውንት ላይ አስገብተው እንደተሰወሩባቸው ኮሚሽኑ ጠቅሷል።

ሌላ አንድ አባት ደግሞ ከሆሮ ጉዱሩ ወለጋ 640 ሺህ ብር በተለያየ ጊዜና አካውንት ላይ ገቢ ካደረጉ በኋላ ተጠርጣሪዎቹ ደብዛቸው መጥፋቱን ለኮሚሽኑ መሰረዳታቸው የገለጸው ኮሚሽኑ፣ ከአዲስ አበባ አንድ መምህር 48 ሺህ ብር በአጭበርባሪዎቹ አካውንት ካስገቡ በኋላ ጉዳዩ ማጭበርበር እንደሆነ ከደረሱበት በኋላ በድጋሚ ላኩ የተባሉትን ተጨማሪ ብር ሳይልኩ ለፖሊስ ማመልከታቸው ገልጸዋል።

ይህንን የወንጀል ተግባር ለመቆጣጠርና ለማክሸፍ ፖሊስ ባደረገው ጥረት አጭበርባሪዎቹ የባንክ አካውንትና ሲም ካርድ የሚያወጡት በሀሰተኛ /Forged/ መታወቂያ እንዲሁም የሚደውሉበት የስልክ መስመርም የጁንታው ቡድን ከዚህ በፊት ለእኩይ ተግባር ባሰራጫቸው ሲም ካርዶች ጭምር መሆኑም አመለክቷል።

በመሆኑም የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ወንጀል ኢንተለጀንስ ዜጎች የዚህ ወንጀል ሰለባ እንዳይሆኑ እያሳሰበ መሰል የማጭበርበር ድርጊት ሲያጋጥም ብሩን ገቢ ከማድረግ አስቀድመው ከቤተሰቦቻቸው ጋር በመነጋገር እና ለፀጥታ አካላት በመጠቆም ህገ-ወጦችን ለህግ አስከባሪ አካላት አሳልፈው መስጠት እንደሚኖርባቸው ማሳሰቡን ከፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽኑ ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡