ጆ ባይደን በሚቀጥለው ሳምንት በይፋ ወደ ነጩ ቤተመንግስት ይገባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

46ኛ የአሜሪካ ፕሬዝዳንት በመሆን የተመረጡት ጆ ባይደን በሚቀጥለው ሳምንት በይፋ ወደ ነጩ ቤተመንግስት ይገባሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በአለ ሲመታቸው በሚከበርበት በዋሽንግተን ከተማም ከ10 ሺህ በላይ የሚሆኑ ወታደሮችም ጆ ባይደንን ያጅባሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ CNBC ዘግቧል፡፡

በቴሌቪዥን በቀጥታ ለህዝብ በሚደርሰው የጆ ባይደን በአለ ሲመት ታዋቂው የፊልም ሰው ቶም ሀንከስ ዝግጅቱን የሚመራው ይሆናል፡፡

በዚህ ዝግጅት ታዋቂ አቀንቃኞች ዝግጅቱን እንደሚያደምቁት የሚጠበቅ ሲሆን ከተጋባዥ ዝነኛ አቀንቃኞች መካከልም ጀስቲን ቲምበርሌክ እና ዲሚ ሎቫቶ ይገኙበታል፡፡

ጀስቲን ቲምበርሌክ በዝግጅቱ አዲስ ስራ እንደሚያቀርብ በቲውተር ገጹ ላይ አስፍሯል፡፡

ከኮሮና ጋር በተገናኝ የሰራው አዲሱ ሙዚቃው የተሸለ ቀን እናያለን የሚል መጠርያም እንደሰጠው ነው ጀስቲን ቲምበርሌክ የተናገረው፡፡

ለ90 ደቂቃ ያህል በሚቆየው የጆ ባይደን በአለ ሲመት የቀድሞ የሀገሪቱ ፕሬዝዳንቶች እና ባለቤቶቻቸው ይታደሙታል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

የዶናልድ ትራምፕ ደጋፊዎችና የነጭ ዘር የበላይነት አቀንቃኞች ፕሬዝዳንታዊ ሽግግሩን እንዳያስተጓጉሉ ከፍተኛ ስጋት ፈጥሯል፡፡

ተሰናባቹ ፕሬዝዳንት ዶናልድ ትራምፕ በጆ ባይደን በአለ ሲመት እንደማይገኙም ከዚህ በፊት ማሳወቃቸው ይታወሳል፡፡