መንግሥት በየክልሉ የተደራጀ ልዩ ኃይል ወደክልሎቹ መደበኛ የፖሊስ ኃይል አልያም የፌደራል ፖሊስና የሀገር መከላከያ ሠራዊት እንዲቀላቅል አሁንም ደግመን እናሳስባለን – ኢዜማ

የዜጎች ሰብዓዊ መብት መከበር በምንም ምክንያት እና በማንኛውም ጊዜ ለድርድር የማይቀርብ ነው!
ኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትህ (ኢዜማ) የተሰጠ ጋዜጣዊ መግለጫ
አምነስቲ ኢንተርናሽናል «ሕግን ከማስከበር ባሻገር» በሚል ርዕስ ባወጣው ዘገባ በኦሮሚያ እና በአማራ ክልል ሁለት አካባቢዎች በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ተፈጽመዋል ያላቸውን የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን ዘርዝሯል። በዘገባው ውስጥ በፀጥታ አስከባሪዎች እርምጃ በአሰቃቂ እና ከህግ ውጪ በሆነ ሁኔታ የዜጎች ሕይወት መጥፋቱን፣ ሴቶች መደፈራቸውን፣ በማቆያ ካምፖች ውስጥ ሰቆቃ መፈፀሙን፣ ከሕግ አግባብ ውጪ እስር መፈጸሙን፣ ዜጎች ከሚኖሩበት እንደተፈናቀሉ እና ንብረታቸው እንደወደመ ተዘርዝሯል። በተጨማሪም በተለያዩ ማኅበረሰቦች
መካከል የእርስበርስ ግጭት ሲከሰት የአካባቢ አስተዳዳሪዎች እና ፀጥታ ኃይሎች የዜጎችን ደኅንነት ከማስጠበቅ ይልቅ በግጭቱ ውስጥ እንደተሳተፉ እንዲሁም ኃላፊነታቸውንም በአግባቡ እንዳልተወጡ ተጠቅሷል። እነዚህ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ጉባዔ በአካባቢው ይፈፀማሉ ብሎ ካወጣው የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች ዘገባ ጋር ተመሳሳይነት አላቸው።
ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ ግልጽ እንዳደረግነው፣ ምንም ሕገ መንግሥታዊ መሰረት የሌለው የክልል ልዩ ኃይል አደረጃጀት የዜጎችን ደህንነት ከማስጠበቅ ይልቅ እራሱን የአንድ ወገን ጠባቂ እና ተከላካይ አድርጎ በመቁጠር ለዜጎች ደህንነት ስጋት ሆኖ መቀጠሉን የሚያሳዩ ተደጋጋሚ
ማስረጃዎች እያየን ነው። ስለዚህም መንግሥት ይህን በየክልሉ የተደራጀ ልዩ ኃይል ወደክልሎቹ መደበኛ የፖሊስ ኃይል አልያም የፌደራል ፖሊስ እና የሀገር መከላከያ ሠራዊት እንዲቀላቅል አሁንም ደግመን እናሳስባለን።